ህዝቡ ለመራጭነት የሚያበቃውን ካርድ ከወዲሁ ሊወስድ ይገባል – አቶ ደስታ ሌዳሞ

መጋቢት 30/2013 (ዋልታ) – ህዝቡ የመራጮች የምዝገባ ጊዜ ገደብ ከማለቁ በፊት ለመራጭነት የሚያበቃውን ካርድ በመውሰድ የሚበጀውን ለመምረጥ ዝግጁ ሊሆን ይገባል ሲሉ የሲዳማ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ደስታ ሌዳሞ አስገነዘቡ።

ርዕሰ መስተዳድሩ አቶ ደስታ ሌዳሞ ለ6ኛው ሀገር አቀፍ ምርጫ ዛሬ በመራጭነት ተመዝግበዋል።

እንደ ኢዜአ ዘገባ በሀዋሳ ታቦር ክፍለ ከተማ ሂጣታ ቀበሌ የምርጫ ጣቢያ ተገኝተው የመራጭነት ካርድ የወሰዱት ርዕሰ መስተዳድር አቶ ደስታ ሌዳሞ እንዳሉት ህብረሰተቡ ለመራጭነት ብቁ የሚያደርገውን ካርድ ከወዲሁ በመውሰድ ይበጀኛል የሚለውን አካል መምረጥ አለበት።

ምርጫ ለሀገሪቱ የዲሞክራሲ ሽግግር የሚኖረው ፋይዳ ላቅ ያለ በመሆኑ የመራጮች ምዝገባ ጊዜ ሊጠናቀቅ የቀረው አጭር ጊዜ እንደሆነ በመረዳት ካርድ መውሰድ እንደሚገባ ገልጸዋል።