ለጤና ሚኒስቴር 1ነጥብ 7 ሚሊየን ዶላር የሚያወጣ መድሃኒት ድጋፍ ተደረገ

ሰኔ 08/2013 (ዋልታ) – የአሜሪካ አለም አቀፍ የተራድኦ ድርጅት ትራንስፎርመር ኤች ዲ አር ፕሮጀክት ከኢንተርናሽናል ሄልዝ ፓርትነር ጋር በመሆን 1 ነጥብ 7 ሚሊዮን ዶላር በላይ ሚገመት ሜቤንዳዞን መድሐኒት ለጤና ሚኒስቴር ድጋፍ አድርጓል፡፡

የጤና ሚኒስቴር ዴኤታ ወይዘሮ ሠሃረላ አብዱላሂ መድሃኒቶቹን በተረከቡበት ወቅት እንደተናገሩት፣ እርዳታው ጤና ሚኒስቴር  የማህበረሰቡን ጤና ለማሻሻል እንደዚሁም ያቀዳቸውንም ተግባራት ለማሳካት እገዛ እንደሚኖረው ተናግረዋል። የተደረገውን ድጋፍም በሚኒስቴር መስርያ ቤቱ ስም አመስግነዋል፡፡

የአሜሪካ አለም አቀፍ የተራድኦ ድርጅት ትራንስፎርመር ኤች ዲ አር ፕሮጀክት ቺፍ ኦፍ ፓርቲ ዶክተር ስንታየሁ ጸጋዬ በበኩላቸው÷ ድጋፉ የእናቶችንና ህጻናት ጤናን ለማሻሻል እና ሌሎች ፕሮግራሞችንም ለመደገፍ እንደሚያግዝ ገልጸዋል።

እርዳታው በዘጠኝ ክልሎች በተለይም ቤንሻንጉል፣ ጋምቤላ፣ አፋርና ሶማሌ ክልሎች የሚዳረስ ይሆናልም ነው ያሉት፡፡

በቀጣይም መሰል ድጋፎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ዶክተር ስንታየሁ መናገራቸውን ከጤና ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡