በመዲናዋ የጦር መሳሪያ ምዝገባ እስከ ህዳር 3 ቀን እንዲቀጥል ተወሰነ

ጥቅምት 30/2014 (ዋልታ) የጦር መሳሪያ ምዝገባው እስከ ህዳር 3 ቀን 2014 ዓ.ም እንደሚቀጥል የአዲስ አበባ ፖሊስ አስታወቀ፡፡

የጦር መሳሪያ በእጁ የሚገኝ ማንኛውም ግለሰብ ፈቃድ ያለውም ሆነ የሌለው የመዲናዋ ነዋሪ በሁሉም ክፍለ ከተሞች እና በስሩ በሚገኙ ፖሊስ ጣቢያዎች እየቀረበ መሳሪያውን እንዲያስመዘግብ ጥሪ መቅረቡ ይታወሳል፡፡

ጥቅምት 23 ቀን 2014 ዓ.ም በተሰጠው መመሪያ የጦር መሳሪያ ያላቸው ግለሰቦች በተራዘመው የጊዜ ገደብ መሰረት እስከ ጥቅምት 27 ቀን 2014 ዓ.ም ድረስ እየቀረቡ ሲያስመዘግቡ መቆየታቸውንም ፖሊስ አስታውቋል፡፡

ምዝገባውን በሃገር አቀፍ ደረጃ ወጥ ለማድረግ መታሰቡን እና አሁንም በተለያዩ ምክንያቶች ያላስመዘገቡ ግለሰቦች ባቀረቡት ጥያቄ መሰረት እስከ አርብ ህዳር 3 ቀን 2014 ዓ.ም እንዲቀጥል የተወሰነ በመሆኑን ገልጿል፡፡

የጦር መሳሪያ ያላስመዘገቡ የመዲናዋ ነዋሪዎች የጊዜ ገደቡ ከመጠናቀቁ በፊት በአቅራቢያችሁ በሚገኙ ፖሊስ ጣቢያዎች እየቀረባችሁ እንድታስመዘግቡ ሲል ጥሪ ማቅረቡን ከአዲስ አበባ ፖሊስ ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡