ኢትዮጵያ በዓባይ ውሃ የመጠቀም መብቷን የሚገድብ ማንኛውንም ዓይነት ስምምነት እንደማትፈርም አስታወቀች

የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ድርድር

መጋቢት 29/2013 (ዋልታ) – ኢትዮጵያ በአባይ ውሃ የመጠቀም መብቷን የሚገድብ ማንኛውንም ዓይነት ስምምነት እንደማትፈርም አስታውቃለች፡፡
በአፍሪካ ህብረት ማዕቀፍ እየተከናወነ የሚገኘው የኢትዮጵያ፣ ሱዳን እና ግብጽ የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ድርድር ስለሚቀጥልበት ሁኔታ ለመመካከር በኪንሻሳ የውጭ ጉዳይ እና የውሃ ሚኒስትሮች ስብሰባ ተካሂዷል፡፡
ስብሰባውን በተመለከተ ኢትዮጵያ ባወጣችው መግለጫ፣ ስብሰባው ያለፉትን ሂደቶች በመገምገም ድርድሩ የሚቀጥልበትን ሂደት ለመወሰን ታስቦ የተዘጋጀ እንደነበር አስታውሳለች።
በስብሰባው መክፈቻ ንግግር ያደረጉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንንም ኢትዮጵያ የአፍሪካ ህብረት የድርድር ሂደት እንዲቀጥል እና በውጤት እንዲጠናቀቅ የበኩሏን ጥረት እንደምታደርግ አሳታውቀዋል።
ዓባይ የድንበር ተሻጋሪ ሀብት እንደመሆኑ የተፋሰሱ ሀገራት ፍትሃዊና ምክንያታዊ መርህን መሰረት ባደረገ አኳኋን የመጠቀም መብት እንዳላቸው ገልፀዋል።
በመሆኑም በተፋሰሱ ላይ የሰፈነው የታችኛው ተፋሰስ ሀገራት ብቸኛ ተጠቃሚነትን የማስቀጠል ፍላጎት መቀየር ያለበትና በትብብር እና መግባባት ሊወሰን እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሕዳሴ ግድብ የትብብር ዕድልን የፈጠረ ሀገራዊ ፕሮጀክት በመሆኑ በድርድር ሂደቱ የተደረሱ የአቋም መቀራረቦችን ከዳር ማድረስ እንደሚገባ አስምረውበታል፡፡
በስብሰባው ሶስቱም ታዛቢዎች ማለትም ደቡብ አፍሪካ፣ አሜሪካ እና የአውሮፓ ህብረት በታዛቢነት እንዲቀጥሉ ስምምነት ተደርሷል።
ኢትዮጵያ ሀገራቱ ሙሉ ባለቤት የሆኑበትን እና የአፍሪካ ህብረት ማዕቀፍን የሚያስጠብቅ የድርድር ሂደት በመደገፍ ታዛቢዎች በሶስቱ ሀገራት በጋራ ስምምነት ሲጠየቁ ብቻ ሃሳብ ማቅረብ ለመፍቀድ ተስማምታለች፡፡
ግብጽ እና ሱዳን ታዛቢዎች ከአፍሪካ ህብረት እኩል ተሳትፎ የማድረግ ሚና ሊሰጣቸው ይገባል በሚል ያቀረቡት ሀሳብ ተቀባይነት እንዳላገኘ ተገልጿል፡፡
የሁለቱ ሀገሮች አካሄድ የአፍሪካ ህብረትን ሚና የሚያሳንስ መሆኑን ነው መግለጫው ያመለከተው።
በስብሰባው ማጠናቀቂያ በዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትርና የአፍሪካ ኅብረት ሥራ አስፈጻሚ ምክር ቤት ሊቀመንበር የቀረበውን ረቂቅ መግለጫ ኢትዮጵያ በመሰረቱ ለመቀበል መስማማቷን ገልጻለች፡፡
በአንፃሩ፣ ግብጽ እና ሱዳን በሁለቱ ቀናት ውይይት ያልተነሱ ጉዳዮችን ካልተካተቱ በሚል ረቂቁን አለመቀበላቸውን አስታውቀዋል፡፡
በመሆኑም፣ ሁለቱ ሀገራት የአፍሪካ ህብረት ሂደትን የሚያሳንስ እና ጉዳዩን ከህብረቱ የሚያወጣ ስልት በመከተል እንዲሁም ምክክር የተደረገባቸውን ጉዳዮች የያዘ መግለጫ አንቀበልም በማለት ድርድሩ አዎንታዊ ውጤት እንዳይኖረው እንቅፋት መሆናቸው ተገልጿል።
የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባወጣው መገለጫ እንዳስታወቀው፣ የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ሁለተኛ ዓመት ሙሌት በተያዘለት የጊዜ ሰሌዳ ይከናወናል፡፡
ሁለቱ ሀገሮች ስምምነት ሳይደረስ ግድቡ መሞላት የለበትም በሚል የሚቀርብ አቋም የሕግ መሰረት የሌለው እንዲሁም የኢትዮጵያን የተፈጥሮ ሀብቷን የመጠቀም መብት የሚጋፋ በመሆኑ ተቀባይነት የለውም ብሏል፡፡
የግድቡ አሞላል እና ተያያዥ የውሃ እለቃቅ ስርዓት ላይ ለመስማማት ኢትዮጵያ በተደጋጋሚ ዝግጁ ብትሆንም ግብጽ እና ሱዳን በግድቡ ላይ የሚደረገው ድርድር እና ውጤቱ የኢትዮጵያን የውሃ ድርሻ የሚገድብ እና አለን የሚሉትን የውሃ ክፍፍል የሚያጸና አስገዳጅ ስምምነት ካልተደረሰ የሚል ግትር አቋም መያዛቸውንም መግለጫው አመልክቷል።
ኢትዮጵያ ፍትሐዊ እና ምክንያታዊ የሆነ የአሁን እና የወደፊት በዓባይ ውሃ የመጠቀም መብቷን የሚያቅብ ማናቸውም ዓይነት ስምምነት እንደማትፈርምም ገልጿል።
ኢትዮጵያ የወቅቱ የአፍሪካ ህብረት ሰብሳቢ እና የዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ፕሬዝዳንት ፌሊክስ ሼሲኬዲ እና ቡድናቸው ድርድሩን ለማስቀጠል ያሳዩትን ብርቱ ጥረት በከፍተኛ አክብሮት እንደምትመለከተው በመግለጫው ተጠቅሷል።
ኢትዮጵያ የድርድሩ ሒደት የሀገራቱን ሙሉ ባለቤትነት በሚያረጋግጥ እና የአፍሪካ ህብረትን የማስተባበር ሚና በተሟላ አኳኋን የሚያስጠብቅ የሶስትዮሽ ድርድር ለመከተል ዝግጁ መሆኗንም አስታውቃለች።
ኢትዮጵያ በአፍሪካ ሕብረት የወቅቱ ሊቀመንበር በሚያቀርቡት ጥሪ በቅርቡ ስብሰባው ይቀጥላል ብላ እንደምትጠብቅም በመግለጫው ተጠቁሟል።