ኢትዮጵያ 2.2 ሚሊየን የኮቪድ 19 ክትባት ተረከበች

የኮቪድ 19 ክትባት
የካቲት 28/2013 (ዋልታ) – ኢትዮጵያ ኮቫክስ ከተሰኘው ዓለምአቀፍ ጥምረት 2 ነጥብ 2 ሚሊየን የኮቪድ-19 ክትባት በዛሬው ዕለት ተረከበች፡፡
የመጀመሪያው ዙር የኮቪድ-19 ክትባት ዛሬ ማለዳ ቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ሲደርስ የጤና ሚኒስትሯ ዶ/ር ሊያ ታደሰን ጨምሮ ከፍተኛ የአፍሪካ ህብረት የአውሮፓ ህብረት እና ሌሎችን የመንግስታቱ የስራ ኃላፊዎች ተገኝተውበታል፡፡
ክትባቱ ወደ ሀገር ውስጥ በመግባቱ እንኳን ደስ አላችሁ መልዕክት ያስተላለፉት የጤና ሚኒስትሯ ዶ/ር ሊያ ታደሰ፣ ክትባቱ ለህክምና ባለሙያዎች፣ ተጓዳኝ በሽታ ላለባቸው የህብረተሰብ ክፍሎችና በዕድሜ ለገፉ አዛውንቶች በቅድሚያ እንደሚሰጥ አስታውቀዋል፡፡
ክትባቱን ለመስጠት የሚያስችሉ የቅድመ ዝግጅት ስራዎች መጠናቀቃቸውንም ገልጸዋል፡፡
(በሀኒ አበበ)