ኢዜማ ከገዢው ፓርቲ የቀረበለትን የአብረን እንሥራ ጥያቄ ተቀበለ

መስከረም 23/2014 (ዋልታ) – የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትሕ /ኢዜማ/ ከገዢው ፓርቲ የቀረበለትን የአብረን እንሥራ ጥያቄ በአብላጫ ድምፅ መቀበሉን አስታወቀ፡፡
ኢዜማ የመጀመሪያ አስቸኳይ ጉባዔውን በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች ከሚገኙ የምርጫ ወረዳዎች የተወከሉ የፓርቲው አባላት በተገኙበት መስከረም 22 እና 23 ቀን 2014 ዓ.ም አካሂዷል።
ፓርቲው በጉባዔው ማጠቃለያ ላይ ባወጣው የአቋም መግለጫ ከገዢው ፓርቲ የቀረበለትን የአብረን እንሥራ ጥያቄን ጨምሮ በ6 አጀንዳዎች ላይ ውሳኔ ማሳለፉን አስታውቋል።
ከገዢው ፓርቲ የቀረበውን የአብረን እንሥራ ጥያቄ በሚመለከት ጉባዔው ሰፊ ጊዜ ወስዶ ከተወያየ በኋላ አሁን ኢትዮጵያ ካለችበት ወቅታዊ ሁኔታ አንፃር ጥያቄውን ተቀብሎ አብሮ ለመሥራት በ536 ድጋፍ፣ 79 ተቃውሞ እና 25 ድምጸ ተዓቅቦ በአብላጫ ድምጽ ውሳኔ ማሳለፉን ከፓርቲው ማህበራዊ ትስስር ገጽ የተገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡
ፓርቲው ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የደንብ ማሻሻያ እንዲያደርግ በተሰጠው አቅጣጫ መሠረት ማሻሻያውን ለጉባዔው አቅርቦ በ595 ድጋፍ፣ 3 ተቃውሞ እና 32 ድምፀ ተዓቅቦ አፅድቆ የተሻሻለው ደንብ ለብሔራዊ ምርጫ ቦርድ እንዲገባ ውሳኔ ተላልፏል።