ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የተሰጠ መግለጫ

ኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ለ6ተኛው አገራዊ ምርጫ የሚያደርገውን ዝግጅት አስመልክቶ የጊዜ ሰሌዳ ማውጣቱ እንዲሁም የተለያዩ ተግባራትን ለማከናውን ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በጋራ እየሰራ እንደሚገኝ ይታወቃል።

ከዚህም መካከል የምርጫ ጸጥታን ማረጋገጥ እንዲሁም የምርጫ ክልል እና የዞን ቢሮዎችን ለመክፈት መስራት ይገኙበታል።

በዚህም መሰረት ቦርዱ በተለያዩ ወቅቶች ከክልል መስተዳድር ሃላፊዎች ጋር ውይይቶችን ያከናወነ ሲሆን በነዚህ ውይይቶች ላይ የምርጫ ኦፕሬሽን መዋቅር እና የክልል መስተዳድሮች የሚጠበቁ ሚናዎችን በዝርዝር አቅርቧል።

በውይይቶቹ በተደረሰው ስምምነት መሰረት ቦርዱ የሚከተሉትን ዋና ዋና ትብብሮች ከክልል መንግስታት የጠየቀ ሲሆን እነሱም በዋናነት

  1. የአዲስ አበባ ከተማ መስተዳድር- 33 የምርጫ ክልል ቢሮዎች እና 3 የዞን ማስተባበሪያ ቢሮዎች እና የስልጠና ቦታዎች
  2. ድሬደዋ ከተማ መስተዳድር- 47 የምርጫ ክልል ቢሮዎች እና 1 የዞን ማስተባበሪያ ቢሮዎች እና የስልጠና ቦታዎች
  3. ሶማሌ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት -72 የምርጫ ክልል ቢሮዎች እና 11 የዞን ማስተባበሪያ ቢሮዎች እና የስልጠና ቦታዎች
  4. ጋምቤላ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት- 14 የምርጫ ክልል ቢሮዎች እና 3 የዞን ማስተባበሪያ ቢሮዎች እና የስልጠና ቦታዎች
  5. ደ/ብ/ብ/ህ ክልላዊ መንግስት እና ሲዳማ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት- 132 የምርጫ ክልል ቢሮዎች እና 17 የዞን ማስተባበሪያ ቢሮዎች እና የስልጠና ቦታዎች
  6. ሃረሪ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት- 3 የምርጫ ክልል ቢሮዎች እና 1 የዞን ማስተባበሪያ ቢሮዎች እና የስልጠና ቦታዎች
  7. አፋር ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት -32 የምርጫ ክልል ቢሮዎች እና 5 የዞን ማስተባበሪያ ቢሮዎች እና የስልጠና ቦታዎች
  8. አማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት- 138 የምርጫ ክልል ቢሮዎች እና 12 የዞን ማስተባበሪያ ቢሮዎች እና የስልጠና ቦታዎች
  9. ኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት- 179 የምርጫ ክልል ቢሮዎች እና 20 የዞን ማስተባበሪያ ቢሮዎች እና የስልጠና ቦታዎች ናቸው።

ቦርዱም በጥያቄው ለክልሎች ለእቅድ እና ለአፈፃፀም ያመቻቸው ዘንድ የምርጫ ክልሎች ዝርዝር እና ቢሮአቸው የሚቋቋምባቸው ከተሞች ዝርዝር፤ የዞን ማስተባበሪዎች ዝርዝር እና ቢሮአቸው የሚቋቋምባቸው ከተሞች ዝርዝር እንዲሁም ቦርዱ ያወጣውን ረቂቅ የምርጫ ሰሌዳ ኮፒ አብሮ አቅርቧል።

ይሁንና ለክልሎች ይህንኑ ለቢሮ መከፈት የሚያስፈልግ ዝግጅት በደብዳቤ በመጠየቅ ለ ጥር 10 ቀን 2013 ዓ.ም እንዲያሳውቁ ጥያቄ ያቀረበ ቢሆንም እስከአሁን ድረስ ይህንን ዝግጅት አስመልክቶ ምላሽ ያቀረበ የክልል መስተዳድር የለም።

በመሆኑም በደብዳቤ የተገለጹት አስፈላጊ የምርጫ ክልል ቢሮዎችን ለመክፈት የሚያስፈልጉ ትብብሮች ለምርጫው ሂደት አስፈላጊነታቸውን በመገንዘብ ክልሎች ትብብራቸውን እንዲያፋጥኑ እንዲሁም በኢትዮጵያ የምርጫ፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባና የምርጫ ስነምግባር አዋጅ 1162/2011 አንቀጽ 161 የተቀመጠውን የመተባበር ግዴታቸውን እንዲወጡ እናሳስባለን።

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ

ጥር 10 ቀን 2013 ዓ.ም