የሩስያ ባለሃብቶች በኢትዮጵያ በኢኖቬሽን፣ በቴክኖሎጂ እና በኢነርጂ ልማት ዘርፍ ለመሳተፍ ፍላጎት እንዳላቸው ተገለጸ

 

የሩስያ ባለሃብቶች በኢትዮጵያ በኢኖቬሽን፣ በቴክኖሎጂ እና በኢነርጂ ልማት ዘርፍ ለመሳተፍ ፍላጎት እንዳላቸው የሩስያ የውጭ ኢኮኖሚ ልማት ኢንቨስተሮች እና ስራ ፈጣሪዎች ማህበር ሊቀመንበር ማረክ ሩስላን ገለጹ።

በሩስያ የውጭ ኢኮኖሚ ልማት ኢንቨስተሮች እና ስራ ፈጣሪዎች ማህበር ሊቀመንበር ማረክ ሩስላን የተመራ የሩስያ የቢዝነስ ልዑካን ቡድን በኢትዮጵያ መዋዕለ ንዋያቸውን ማፍሰስ በሚችሉባቸው መስኮች ዙሪያ ከኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ጋር መክረዋል።

የልዑካን ቡድኑ የሩስያ ባለሃብቶች በአገሪቱ እየተካሄደ ባለው የዲጂታል እና አረንጓዴ ኢኮኖሚ ልማት ላይ በመሳተፍ ያካበቱትን ልምድ በኢትዮጵያም ለመድገም ዝግጁ መሆናቸውን አረጋግጠዋል።

የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዶክተር አብረሃም በላይ፥ የኒውክለር ኢነርጂን በማልማት መስክ በትብበር ስራዎች እየተሰሩ ስለመሆናቸው አብራርተዋል።

ኢትዮጵያ የዲጂታል ኢኮኖሚን ለመገንባትና ለውጭ ባለሃብቶች ምቹ ሁኔታን ለመፍጠር መንግስት እያደረገ ስላለው የማሻሻያ ስራዎችም ማብራሪያ ሰጥተዋል።

የልዑካን ቡድኑ መሪ ማረክ ሩስላን የሩስያ ባለሃብቶች በቴክኖሎጂ ፣ኢኖቬሽን እና በኢነርጂ ልማት ዘርፍ ለመሳተፍ ከፍተኛ ፍላጎት እንዳላቸው እና በኢትዮጵያ እየተካሄደ ያለውን የለውጥ እንቅስቃሴም እንደሚያደንቁ ተናግረዋል።

በውይይቱ ኢትዮጵያ ያፀደቀችው የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ስትራቴጂ እና በክለሳ ላይ በሚገኘው የሳይንስ ኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ፖሊሲ ላይ እየተደረጉ ባሉ እንቅስቀሴዎች ላይም ማብራሪያ ተሰጥቷል።

በፍጥነት ወደ ተግባር ለመግባት እንዲቻል ከሚኒስቴር መስሪያቤቱ እና ከልዑካን ቡድኑ የተውጣጣ ቡድን የተቋቋመ ሲሆን፥ ለቡድኑ በጥናት ላይ የተመሰረተ የድርጊት መርሃ ግብር እንዲያቀርብ መመሪያ መሰጠቱን ከኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።