የተሃድሶ ስልጠና የወሰዱ የትግራይ ክልል ተወላጅ ፖሊስ አባላት በክልሉ ስምሪት ተሰጣቸው

የአጭር ጊዜ የተሃድሶ ስልጠና የተሰጣቸው የትግራይ ክልል ተወላጅ ፖሊስ አባላት በትግራይ ክልል ህዝብን እንዲያገለግሉ ስምሪት መስጠቱን የፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን አስታወቀ።
ሕግ ማስከበር ዘመቻውን ተከትሎ በክልሉ ሰላምና መረጋት እንዲሰፍን፣ የክልሉን ጸጥታ ተቋማት ለማደራጀትና ቀሪ የጁንታ አመራሮችን አድኖ ለፍርድ ለማቅረብ እየሰራ መሆኑን ኮሚሽኑ ለኢዜአ በላከው መግለጫ አስታውቋል።
በክልሉ ሁሉም አካባቢዎች ሰላምና ጸጥታን ለማስፈንና ወንጀለኞችን የማደን ተልዕኮ በአገር መከላከያ ሰራዊትና በፌዴራል ፖሊስ የሕይወት መስዋዕትነት በተቀናጀ መንገድ በብቃት እየተወጡ መሆኑንም በመግለጫው አመልክቷል።
በዚህም ህዝቡን በሰላምና በፍትህ ለማርካት የክልሉ ተወላጅ የፌዴራል ፖሊስ አባላት ተልዕኳቸውን በብቃት እንዲወጡ የተሃድሶ ስልጠና በመስጠት ወደ ክልሉ ስምሪት እንደተሰጣቸው ኮሚሽኑ ጠቁሟል።
“በአፍ መፍቻ ቋንቋ ተናጋሪ ፖሊስ አባላትን አሰልጥኖ ወደ ክልሉ ማሰማራቱ ህብረተሰቡ ያጋጠሙትን ችግሮች በፍጥነት ለመቅረፍና የተበታተነውን የጥፋት ቡድን ለማጽዳት ስምሪቱ ወቅቱን የጠበቀ ነው” ብሏል።
በጁንታው የሀሰት ፕሮፓጋንዳ የተጎዳ ህዝብ ወደቀደመ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅሰቃሴው በአስተማማኝ ሁኔታ እንዲመለስ የፖሊስ አባላቱ ግዳጃቸውን በጥንቃቄና ትኩረት በተሞላበት አግባብ እንዲወጡ ሃላፊነት እንደተጣለባቸው ኮሚሽኑ ገልጿል።