የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ በናይሮቢ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ከፈተ

ጥቅምት 5/2014 (ዋልታ) የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ በኬንያ ናይሮቢ የሚገኙ የተለያዩ የሃይማኖት ተቋማትን የሚያካትት ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት መክፈቱ ተገለጸ።

ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤቱ ትናንት ሲከፈት የኢትዮጵያ ሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ ዋና ፀሐፊ ሊቀ-ትጉኃን ቀሲስ ታጋይ ታደለ፣ በኬኒያ የኢትዮጵያ አምባሳደር መለስ ዓለምና የኬኒያ የሃይማኖት የተቋማት ምክር ቤት ፕሬዚዳንት አባ ጆሴፍ ሙቲ መገኘታቸውን ኢዜአ ዘግቧል።

የኢትዮጵያ ሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ ዋና ፀሐፊ ሊቀ ትጉኃን ቀሲስ ታጋይ ታደለ፥ የጽህፈት ቤቱ መከፈት በኬንያ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን በጋራ ሃይማኖታዊና ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ እንዲግባቡ አስተዋጽኦ ያደርጋል ብለዋል።

ጽህፈት ቤቱ ከኬንያ የሃይማኖት ተቋም ምክር ቤት ጋር በመቀናጀት የሁለቱን ሀገራት ሕዝቦች ትስስር ለማጠናከር እንደሚሰራም ተናግረዋል።

በኬንያ የኢትዮጵያ አምባሳደር መለስ ዓለም÷ የጽህፈት ቤቱ መከፈት የሁለቱን ሀገራት ህዝቦች አንድነት ይበልጥ ያጠናክራል ብለዋል።

የኬኒያ የሃይማኖት ተቋማት ምክር ቤት ፕሬዚዳንት አባ ጆሴፍ ሙቲ÷ ምክር ቤታቸው ለኢትዮጵያ ሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ ቀደም ሲል በዋሺንግተን ዲሲ እና ሮም ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤቶች መክፈቱ ይታወሳል።