የቻይና ንግድ ሳምንት በኢትዮጵያ ተከፈተ

የቻይናና የኢትዮጵያን  የንግድ ግንኙነትን  የማጎልበት አቅም ያለው የቻይና ንግድ ሳምንት በትናንትው ዕለት  በአዲስ አበባ ተከፈተ ።    

የቻይና  የንግድ ሳምንት ከሰኔ 27  እስከ ሰኔ 29 ድረስ  በኃይል ፣ በኤሌክትሪክ ሥራ ፣ በግንባታ፣ በማሽን ፣ በአልባሳት ፣በጨርቃጨርቅ ፣ ጤናና ውበት ዘርፎች  የተሠማሩ  38  የቻይና ትልልቅ ኩባንያዎችን  በማሳተፍ እየተካሄደ  ይገኛል ።

የቻይና የንግድ ሳምንት በቻይና የንግድ ምክር ቤትና በቻይና ዓለም አቀፍ የንግድ ምክር ቤት ድጋፍ እየተካሄደ መሆኑን ተመልክቷል ።        

ንግድ ሳምንቱ አስተባባሪ ሚቼል ሜይሪክ እንደተናገሩት በአዲስ አበባ የተከፈተው  የቻይና ንግድ ሳምንት  በአጠቃላይ 38 የሚሆኑ  የቻይና የንግድ ተቋማት እየተሳተፉበት ሲሆን ምርትና አገልግሎታቸውን ለኢትዮጵያ  ገበያ እያስተዋወቁ ነው ብለዋል  ።  

እንደ ሜይሪክ ገለጻ የንግድ ትርኢቱ የአገር ውስጥ የንግድ ማህበረሰብ ከቻይና ትልልቅ የንግድ ተቋማትና ኩባንያዎች   ጋር  የጠበቀ የንግድ  ግንኙነት እንዲመሠርቱ  ምቹ ሁኔታ  ይፈጥራል ።      

በኢትዮጵያ በዘንድሮ የበጀት ዓመት ባለፉት ስድስት ወራት  ከተጀመሩ 121 የውጭ  የኢንቨስትመንት ፕሮጀክቶች  ውስጥ  40  የሚሆኑት በቻይና ኩባንያዎች የሚከናወኑ ሲሆኑ  በአጠቃላይ  ከ 3 ቢሊዮን ብር በላይ  ካፒታል የሚካሄዱ ናቸው ብለዋል አስተባባሪው ።  

ቻይና  በኢትዮጵያ የምታደርገው የኢንቨስትመንት ተሳትፎ ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ በመምጣቱ  ዓመታዊ የቻይና የንግድ ሳምንትን በኢትዮጵያ ለማዘጋጀት ዕቅድ ተይዟል ።

ለሦስት  ቀናት   በሚካሄደው የቻይና የንግድ ሳምንት አውደ ርዕይ  ከ3ሺህ በላይ ኢትዮጵያውያን ይጎበኙታል ተብሎ ይጠበቃል ።