6ኛው ሀገራዊ ምርጫ ዴሞክራሲያዊ እንዲሆን የመገናኛ ብዙሃን ሚና ከፍተኛ መሆኑ ተገለጸ

ሚያዝያ 26/2013 (ዋልታ) – በመጪው ግንቦት ወር የሚካሄደው 6ኛው ሀገራዊ ምርጫ ሰላማዊ፣ ዴሞክራሲያዊና ተዓማኒ እንዲሆን መገናኛ ብዙሃን ከፍተኛ ድርሻ እንዳላቸው ተገልጿል፡፡

በሰላም ሚኒስቴር አዘጋጅነት “የመገናኛ ብዙሃን ሚና በ6ኛው ሃገራዊ ምርጫ “በሚል መሪ ሃሳብ ከባለድረሻ አካላት ጋር የምክክር መድረክ እየተካሄደ ይገኛል፡፡

መገናኛ ብዙሃን በምርጫ ሂደቱ ላይ በማወቅና በመረዳት በመረጃ ላይ የተመሠረተ ዘገባ በመስራት ህዝቡ ዴሞክራሲያዊ መብቱን ተጠቅሞ መምረጥ እንዲችል ኃላፊነታቸውን መወጣት እንዳለባቸው ተመላክቷል፡፡

መገናኛ ብዙሃን የምርጫ ህግና መመሪያን በተግባር በማዋል ለምርጫው ሰላማዊነት መሥራት እንደሚገባቸውም ነው የተገለጸው፡፡

“የመገናኛ ብዙሃን ሚና በ6ኛው ሃገራዊ ምርጫ” የምክክር መድረክ ላይ ምርጫ ሰላማዊ፣ ዴሞክራሲያዊና ተዓማኒ እንዲሆን የመገናኛ ብዙሃን ሚና ምንድን ነው በሚል ሀሳብ ላይ በቀረቡት አራት ጽሑፎች ላይ ውይይት እየተደረገ ነው።

(በምንይሉ ደስይበለው)