ጄኔራል ብርሃኑ ጁላ የአየር ወለድ ማሰልጠኛ ህንጻ ግንባታ መሰረተ ድንጋይ አስቀመጡ

 

የካቲት 24/2013(ዋልታ) – የኢፌዴሪ ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም ጄኔራል ብርሃኑ ጁላ በልዩ ዘመቻዎች ኃይል ማሰልጠኛ ማዕከል ስር በሚገኘው የአየር ወለድ ትምህርት ቤት አዲስ ህንጻ ግንባታ መሰረተ ድንጋይ በቢሸፍቱ አየር ኃይል ጊቢ አስቀምጠዋል።

የሚገነባው ህንጻ የትምህርት ቤቱን አቅም ለማጠናከር የሚያገለግል መሆኑ ታውቋል።

ህንጻው በ170 ሚሊዮን ብር ወጪ የሚገነባ ሲሆን በአንድ አመት ውስጥ ተሰርቶ እንደሚጠናቀቅም ተነግሯል።

ከዚህ በተጨማሪም አጠቃላይ የአየር ወለድ የስልጠና ሂደት ጉብኝት ተደርጓል።

በዛሬው እለት የልዩ ዘመቻዎች ኃይል ማሰልጠኛ የአየር ወለድ ስልጠና ማጠናቀቂያ የአየር ወለድ ዝላይና የተኩስ ትርኢት አካሒዷል።

ከተቋቋመ 60 ዓመታትን ያስቆጠረው አየር ወለዱ አዲሱ የህንጻ ግንባታ ዘመናዊ የመሰረተ ልማት እንዲኖረው ያስችላል ተብሏል።
(ምንጭ፡- ኢዜአ)