የትም አያደርስም!

በአገራችን ውስጥ አንዳንድ በተሳሳተ መንገድ የሚጓዙ ነጋዴዎች በሚፈጥሩት ተገቢ ያልሆነ ትርፍ የማካበት ሁኔታ ህገ ወጥ የንግድ ስርዓት እየተስተዋለ ነው። ከግብይት ስርዓቱ ያፈነገጡ ሁኔታዎችም እየታዩ ነው። በዚህም ሳቢያ የኑሮ ውድነት እንዲፈጠር ምክንያት ያልሆኑ ምክንያቶች ሲቀርቡ እየተስተዋሉ ነው። ህዝቡም ምክንያታዊ ያልሆነ የዋጋ ጭማሪ እየተፈጠረበት መሆኑን እየገለጸ ነው።

መንግስት የንግድ ስርዓቱ ህዝቡን በሚጠቅም መልኩ እንዲመራ ብርቱ ጥረት እያደረገ ባለበት በአሁኑ የለውጥ ወቅት፣ አንዳንድ ስግብግብ ነጋዴዎች ግን የግበይት ስርዓቱንና የዋጋ ተመንን ባልተከተለ መልኩ እያከናወኑት ያሉት አላስፈላጊ ጥቅምን የማጋበስ ተግባር የትም የሚያደርስ አይደለም። ህገ ወጥ የንግድ ግብይትና ህግና ስርዓትን ያልተከተለ ትርፍ የማጋበስ አካሄድ አገርንና ህዝብን የሚጎዳ ነው። ስለሆነም መንግስት ይህን ችግር በየጊዜው እየፈታና ወደፊትም የሚፈታ ቢሆንም፣ ህብረተሰቡ በተግባሩ ላይ የሚሳተፉ ነጋዴዎችን በማጋለጥ ከድርጊታቸው እንዲቆጠቡ ሊታገላቸው ይገባል።

እንደሚታወቀው ሁሉ መንግስት የዋጋ ግሽበትን ለማረጋጋት ተከታታይ የሆኑ እርምጃዎችን በመውሰድ የህዝቡን ጥያቄ እየመለሰ መጥቷል። የዋጋ ግሽበቱ ከፍተኛ በነበረባቸው በተለያዩ ወቅት፤ ህብረተሰቡ እንዳይጎዳ ስግብግብ ነጋዴዎች ላይ እርምጃ በመውሰድ እንዲሁም መሰረታዊ የሆኑ የፍጆታ ዕቃዎችን ራሱ በማስገባትና በሸማቾች ማህበራት አማካኝነት ሲያከፋፍል ቆይቷል።

በተጨማሪም ህብረተሰቡ በተመጣጣኝ ዋጋ የሚገዛበትን እንደ ጅምላ አቅራቢ ድርጅቶችን በመክፈት የህዝቡን ጥያቄዎች የመለሰና በመመለስ ላይ ይገኛል። ይህ ሁኔታም ተጠናክሮ ይቀጥላል። አሁን በምንገኝበት የለውጥ ሂደት ውስጥ ስግብግብ ነጋዴዎች ያለ አንዳች ምክንያት በህብረተሰቡ ላይ ዋጋ እየጫኑ ነው። ይህ ፈፅሞ ተቀባይነት ያው ጉዳይ አይደለም።

በአሁኑ ሰዓት ከውጭ የመጡ ምርቶችን በመጋዘን አከማችተው ምክንያታዊ ያልሆነ የዋጋ ጭማሪ በሚያደርጉ ነጋዴዎች ላይ ቁጥጥር እየተደረገ ነው። እርምጃ የመውሰድ ስራውም ተጠናክሮ ይቀጥላል። ገበያውን ለማረጋጋት የጅምላ መሸጫ ሱቆች መሰረታዊ ሸቀጦችን በበቂ ሁኔታ እንዲያቀርብ ይደረጋል።

አሁን ባለንበት ሁኔታ የዋጋ ንረት እንዳይከሰት ለምርት መጠኑ ማደግ መንግስት ከፍተኛ ተግባራት ፈፅሟል። አርሶ አደሩ ምርጥ ዘርን፣ ማዳበሪያንና ሌሎች አቅርቦቶችን በበቂ ሁኔታ አግኝቶ ወደ ምርት ተግባር እንዲገባ እያደረገ ነው። እንዲሁም ለአርሶ አደሩ ልዩ ልዩ የቴክኒክ ድጋፎችን የመስጠት ስራዎችን በመከወን ውጤታማ ተግባራትን በመከወን የኑሮ ውድነት እንዳይከሰት እያደረገ ነው

በተጨማሪም የባንኮች የፋይናንስ ሥርዓት የማስተካከል ሁኔታና የዜጎች የቁጠባ አቅም እንዲያሳድጉ በመደረጉ ሳቢያ የዋጋ ንረቱን ለማርገብ ጥረት በማድረግ ላይ ይገኛል። ከዚህ ጎን ለጎንም የብድር ስርዓቱን የመቆጣጠር ተግባር በገበያው ውስጥ ከፍተኛ ገንዘብ መረጨቱ የዋጋ ንረት እንዲስተካከል የሚያደርገው የቁጥጥር ዘዴ ችግሩን ለመቋቋም የሚያስችል እንደሆነ ስለታመነበት ተግባሩ እየተከናወነ ነው።

መንግስት የገበያ ሁኔታውን ለማረጋጋት ሲል ከራሱ ካዝና በመደጎምም ይሁን ሸቀጦች ህዝቡን እንዳይጎዱ ከቀረጥ ነጻ እንዲገቡ እያደረገ መሆኑ በበጀቱና በገቢው ላይ ቀላል የማይባል ተፅዕኖ የሚያሳርፍ መሆኑ ግልፅ ነው። ሆኖም እነዚህን ተፅዕኖዎች ቢኖሩም ፣ ተገቢ እርምጃዎችን ከመውሰድ ወደ ኋላ አላለም። ይህ ደግሞ አዲሱ አመራር ምን ያህል ለህዝቡ የሚያሳይ ነው።

አዲሱ አመራር የኑሮ ውድነቱን ለማርገብ የተለያዩ እርምጃዎች በመውሰድ የአገራችን የልማት እንቅስቃሴ ተጠናክሮ እንዲቀጥል እያደረገ ነው። በአሁኑ ወቅት እየወሰዳቸው ካሉ ርምጃዎች መካከል የብድር ስርዓቱን መቆጣጠር መቻሉ እንዲሁም ከነጻ ገበያ ሥርዓቱ ጋር ተያይዞ በገበያው ውስጥ ያለው የብር ተመን ንረት የኑሮ ውድነት እንዳይፈጠር ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑ ከብዙ በጥቂቱ የሚጠቀሱ ናቸው።

እርግጥ ከንግዱ ማህበረሰብ ውስጥ የራሳቸውን ፍላጎት ለማርካት ብቻ በዋጋ በመመሳጠር ክፍተት ሲፈጥሩ የቆዩበት የአንዳንድ ስግብግብ ነጋዴዎች የኮንትሮባንድ አሰራር ሁኔታን እየፈጠሩ ነው። ስኳር፣ ዘይት፣ ስንዴ በመሳሰሉ መሰረታዊ የፍጆታ እቃዎች ላይም የኮንትሮባንድ እንቅስቃሴዎች እየተስተዋሉ ነው።

እነዚህ እንቅስቃሴዎች መልሰው የሚጎዱት ህብረተሰቡን ነው። በመሆኑም ህብረተሰቡ ምንም ዓይነት ከህገ ወጥ የንግድ ስርዓት ጋር የተያያዙ ጉዳዩችን ሲመለከት ያለ አንዳች ማመንታት እርምጃ እንዲወሰድ ማመልከት ይኖርበታል። ምክንያቱም ችግሩ መልሶ ተጎጂ የሚያደርገው ራሱን ስለሆነ ነው።

ኢትዮጵያ የምታመርታቸው ምርቶች እንዲሁም ከውጭ የምታስገባቸው እቃዎች በኮንትሮባንድ ገበያ ላይ መዋል አይኖርባቸውም። ምንም ዓይነት የምርት ሂደት ከህጋዊ አሰራሩ ውጭ ግብይት ሊካሄድበት አይገባም። ህብረተሰቡ አምርሮ ሊታገላቸው ይገባል።

በተለይም መሰረታዊ የፍጆታ ሸቀጦች በስውር እጅ በኮንትሮባንድ ከቦታ ቦታ እየተዘዋወሩ በውድ ዋጋ ሲቸበቸቡ እንዲሁም ባልተገባ ሁኔታ የዋጋ ንረት ሲከሰት ህዝቡ በቸልታ  ማለፍ አይኖርበትም። የድርጊቱ ፈጻሚዎች ህግ ፊት እንዲቀርቡ ተገቢውን ጥቆማ መስጠት ይኖርበታል።

በአሁኑ ሰዓት መንግስት የኑሮ ውድነቱን ለመፍታት ብርቱ ጥረት እያደረገ መሆኑ ግልፅ ነው። ይሁን እንጂ መንግስት ብቻውን የሚያመጣው ለውጥ አይኖርም። በአንድ እጅ ማጨበጨብ ይሆናል። ስለሆነም ችግሩን ለመከላከል የህብረተሰቡ ወሳኝ ሚናውን መወጣት ይኖርበታል።

አላስፈላጊ የኑሮ ውድነት በሚፈጥሩ ስግብግብ ነጋዴዎች ሳቢያ ህብረተሰቡ ይጎዳል። ህገ ወጥ ግብይቱም ይሁን ተገቢ ያልሆነ የዋጋ ቁለላ የህዝቡን የኑሮ ሁኔታ የሚያንር ዜጎችን ምሬት ውስጥ እንዲገቡ የሚያደርግ ነው።

ስለሆነም ህዝቡ ራሱን ከእንዲህ ዓይነት የንግድ ሳቦታጅ የሚፈፅሙ ነጋዴዎች መጠበቅና ህጋዊው አሰራርና ግብይት እንዲሰፍን ከመንግስት ጎን ተሰልፎ የበኩሉን ጥረት ማድረግ ይኖርበታል። በዚህም ህብረተሰቡ ህገ ወጥ ግብይትና አላስፈላጊ የዋጋ ንረት ከህዝብ ዓይን እንደማያመልጥና የትም የማያደርስ ተግባር መሆኑን በተለያዩ ምክንያቶች በኢኮኖሚ ሳቦታጅ ወይም በስግብግብነት የተሰለፉ ሃይሎችን በማጋለጥ ሊታገላቸው ይገባል።