የበጎ ሥራ አገልግሎትና ወጣቱ

የበጎ ሥራ አገልግሎት ከስሙ ለማስተዋል እንደሚቻለው ሰዎች በራሳቸው ፍላጎት በመነሳት ያለምንም ክፍያ የሚያከናውኑት መልካም ተግባር ነው።በዚህ ተግባር ላይ የሚሳተፉ ሰዎች የሚያገኙት ትልቁ ነገር የህሊና እርካታ  ነው። የበጎ ሥራ አገልግሎት በሀገራችን  ሲጀመር ሲቁዋረጥ  ቢቆይም የሚፈለገው ያህል ግን እየተሠራበት ነው ለማለት አያስደፍርም። በዚህ አገልግሎት የዓለም ሀገራት በጣም ውጤታማ መሆንም ችለዋል ። በሀገራችንም አሁን መንግሥት ትኩረት ሰጥቶት ሊሠራበት መንገዶች እየተመቻቸ መሆኑን ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትሩ በቅርቡ መግለፃቸው ይታወሳል።ወቅቱም የክረምት ወቅት ከመሆኑ የተነሳ በዚህ ወቅት ብዙ ወጣቶች በእረፍት ላይ ስለሚሆኑ የተለያዩ የበጎ ሥራ አገልግሎቶች ላይ ለመሳተፍ እየተዘጋጁ ይገኛሉ።መንግሥትም ይህንን የወጣቶችን ተነሳሽነት በመመልከት የተለያዩ ድጋፎችን በማድረግ እያበረታታቸው ይገኛል።

ይህ ተግባር ወጣቶች ለሀገራቸው የሚጠበቅባቸውን ሀላፊነትን እንዲወጡና የሀላፊነት ስሜት እንዲሰማቸው ከማድረግ አንፃር ከፍተኛ ሚናን ይጫወታል።ከዚህ በተጨማሪም አሁን ላይ ሀገራችን በጀመረችው የለውጥ ሂደት በማስቀጠል ረገድ እነዚህ በጎ ፍቃደኛ ወጣቶች ለውጥ ያመጣሉ ተብሎ ይጠበቃል።ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ እንደተናገሩት“የአማራው ወጣት ትግራይ ላይ ሄዶ የትግራዩም ኦሮሚያ ላይ የኦሮምያውም ደቡብ ላይ ከሚሰጡት አገልግሎት በዘለለ የባህል ልውውጥ ቢያደርጉ የተሻለ አንድነት ላይ መድረስ ይቻላል”በማለት ወጣቶችኝ በበጎ ሥራ አገልግሎቶች ላይ ማሳተፍ ለሀገራችን ዕድገትና ሰላምን ለማምጣት ከፍተኛ አስተዋፅዖ አላቸው።ወጣቶች ብዙ ነገሮችን መቀየር ይችላሉ ነገር ግን ወጣቱን ለበጎ ሥራ ማነሳሳት ላይ የሚቀሩ ነገሮች አሉ እንዲሁም ለበጎ ሥራ ተብለው የሚመደቡ በጀቶች በተገቢው ቦታ መዋላቸውን  በተገቢው ሁኔታ የሚከታተል አካል ሊኖር ይገባል።ባለፉት ዓመታት የተለያዩ ወጣቶች በተለያዩ የበጎ ሥራዎች ላይ መሳተፋቸው ይታወቃል ነገር ግን የተሠሩ ሥራዎች ብዙም አጥጋቢ ናቸው ለማለት አያስደፍርም ።ህብረተሰቡም ስለ በጎ ሥራዎች ያለው ግንዛቤ አናሳ ስለነበረ ውጤታማ አልነበረም። በተጨማሪም ወጣቱ እንዴትና በምን አይነት ሁኔታና መስፈርት የበጎ ሥራዎች ላይ መሳተፍ እንደሚችሉና ምን ምን ነገሮችን ማሟላት እንደሚገባ ግልፅ መረጃ ሊያገኙ ይገባል።

የወጣቶችና ስፖርት ሚኒስቴር በያዝነው የበጀት ዓመት ከ13.6 ሚሊዮን በላይ ወጣቶችን በበጎ ፍቃድ አገልግሎቶች ላይ ለማሳተፍ ተዘጋጅተዋል።እነዚህ ወጣቶችም ከ26-30 ሚሊዮን ዜጎችን ማገልገል እንደሚችሉ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ባወጣው መረጃ ላይ መግለፅ ችለዋል።ብዙውን  ጊዜ በዚህ የበጎ ፍቃድ  አገልግሎቶች ላይ የሚሳተፉት ከከፍተኛ የትምህርት ተቋማትና ከሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች የተውጣጡ ተማሪዎች ናቸው።ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ባወጣው መረጃ ላይ በ2010 የበጀት ዓመት መጠናቀቂያ የክረምት ወራት ወጣቶች በ14 የሥራ መስኮች ላይ ይሳተፋሉ ተብሎ ይጠበቃል።ከተለያዩ መስኮች ውስጥ ጥቂቶቹ በጤናው መስክ ፣በትምህርት፣በግብርናና በከተማ ፅዳት በመሳሰሉት መስኮች ላይ ወጣቶች በትኩረት ይሳተፋሉ። በተጨማሪም እነዚህ ወጣቶች በዘጠኙም ክልሎችና በሁለቱ ከተማ መስተዳዳሮች ላይ ይሳተፋሉ።

ይህን በወጣቶች የተጀመረውን የበጎ ሥራ አገልግሎች ቀልጣፋና ውጤታማ ለማድረግ የሚመለከታቸው አካላት ሁሉ ለበጎ ፍቃደኞች የሚስፈልጉ ቁሳቁሶችንና ሌሎች ነገሮችን በማሟላት በተሰማሩበት መስኮች ሁሉ ውጤታማ እንዲሆኑ ማበረታታት ይገባቸዋል።