የአመለካከት ለውጡ

በአገራችን እየተካሄደ ያለው የፍቅር፣ የአንድነትና የመደመር ጉዞ በኢትዮጵያውያን መካከል ለዓመታት ሰፍኖ የነበረውን ጥላቻ አስወግዶ በምትኩ ይቅርታንና ፍቅርን በማስፈን አንድነትን ማጠናከር አስችሏል። ይህ ሁኔታ በአገራችን አንጻራዊ ሰላም እንዲኖር፣ ህዝቧም ከሰቀቀንና ከፍርሃት ቆፈን ተላቆ በልማት ላይ እንዲያተኩር እንዲሁም በጠላትነትና በጥርጣሬ ዓይን ሲተያዩ ከቆዩ አጎራባች አገራት ጋር መልካም ጉርብትናንና ትስስርን ማጥበቅ የቻለ ነው።

የኢትዮጵያ የለውጥ ጉዞ ለአገራችን ብቻ ሳይሆን ለክፍለ አህጉሩም ጭምር የዘላቂ ሰላም፣ የልማትና የብልጽግና መሰረት ጥሏል። በአገራችን በአሁኑ ሰዓት እየተወሰዱ ያሉት እርምጃዎችና የመጡት ለውጦች የዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ለኢትዮጵያ ያለውን አመለካከት እንዲለውጥ ያስቻሉ ናቸው።

የአመለካከት ለውጡ ከቃላት ድጋፍ በላይ በተግባር የታዩ ውጤቶችን አምጥቷል። ለዚህም የውጭ ባለሃብቶች መተማመንን በማጠናከር ኢንቨስትመንትን መሳብ እንዲሁም ከአገሮችና ከዓለም አቀፍ ተቋማት ጋር የልማት ትብብርን ማጠናከር ችሏል።

እንደሚታወቀው ሁሉ የኢትዮጵያ መንግስት መርሁ ሰላም ነው። በዚህም ኢንቨስትመንትንና ቱሪዝምን መሳብ ችሏል። በአንድ አገር ውስጥ ቱሪዝምም ሆነ ኢንቨስትመንት ሊስፋፉና ሊያድጉ የሚችሉት አስተማማኝ ሰላምና ለዘርፎቹ ምቹ የሆነ የፖሊሲ አቅጣጫ ሲኖር ነው።

መንግስትና ህዝቡ የሀገሪቱን ሰላም በአንፃራዊ የሰላም መሰረት ላይ ለማቆም ባረደጉት ጥረት እንዲሁም መንግስት ለቱሪዝምም ሆነ ለኢንቨስትመንት ምቹ የሆነ የፖሊሲ አቅጣጫን በመከተሉ፤ ሁለቱም ዘርፎች ከፍተኛ የሆነ እመርታ እየመጣ ነው።

ከቃል ባሻገር ድጋፍ የሚያደርጉልን አገራትም እየታዩ ነው። ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ በአጭር ጊዜ ውስጥ ባመጡት የዲፕሎማሲ ድል ሶስት ቢሊዮን ዶላር ድጋፍና ኢንቨስትመንት ማግኘታችን የዚህ አባባል አስረጅ ነው።

በጠቅላይ ሚኒስትሩ እየተከናወነ ያለው ይህ የኢኮኖሚ ዲፕሎማሲ ኢትዮጵያ ቀጥተኛ የውጭ ኢንቨስትመንትን እንድትስብ ያደረጋትና ወደፊትም የአፍሪካ የኢንቨስትመንት ማዕከል እንድትሆን በማስቻል ረገድ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ሊያበረክት የሚችል ነው።

እንደሚታወቀው ሁሉ የኢትዮጵያ የውጭ ግንኙነት መርህ የአገሪቱን ገፅታ ከመለወጡ ባሻገር፤ በአፍሪካ ብቻ ሳይሆን በዓለም አቀፍ መድረኮችም ተሰሚነቷንና ተፅዕኖ ፈጣሪነቷን ከፍ እንዲል አድርጓል።

አገራችን እያካሄደች ያለው ዲፕሎማሲ ስኬት አንዱ ማሳያ እየተመዘገበ ያለው የኢኮኖሚ ዕድገት ነው። ይህ ዕድገት ልማትን በመደገፍ ረገድ የሚጫወተው ሚና ከፍተኛ ነው። እርግጥ ማንኛውም የውጭ ግንኙነት ስራ ምን ያህል ለአንድ ሀአር ልማት ለማምጣት የውጭ ቀጥተኛና ቀጥተኛ ያልሆነ ኢንቨስትመንትን በመሳብ ረገድ አስተዋፅኦ አድርጓል ከሚል አኳያ የሚታይ ነው። ከውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት ባሻገር ጠቅላይ ሚኒስትሩ ራሳቸው በአካል እየተሳተፉበት የሚገኙት የኢኮኖሚ ዲፕሎማሲ በአገራችን ላይ መተማመን ፈጥሯል።

በእነዚህ ጥረቶች በአሁኑ ወቅት በተለያዩ የኢንቨስትመንት መስኮች በተለይም በግብርና፣ በማኑፋክቸሪንግና ኢንዱስትሪ ዘርፎች የተሰማሩ የውጭ ባለሀብቶች ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እያሻቀበ መጥቷል። አገሪቱ ለኢንቨስትመንት ምቹ መሆኗን የተገነዘቡ በርካታ የውጭ ኩባንያዎችና ባለሃብቶች መዋዕለ ንዋያቸውን ለማፍሰስ መተማመንን አሳድረዋል።

እየተካሄደ ያለው የኢኮኖሚ ዲፕሎማሲው ጥረት ቀጥተኛ የውጭ ምንዛሬን ከማምጣት ባሻገር በአገር ውስጥ የሚከናወኑ የልማት ፕሮጀክቶችንም እየደገፈ ነው። ኢትዮጵያ የምታከናውነው የልማት ፕሮጀክቶችም ኢኮኖሚውን እንዲደግፉ እየተደረገ ነው።

ታዲያ የኢትዮጵያን በጎ ጎን ማስተዋወቅና የምናከናውናቸውን አገራዊ የልማት ፕሮጀክቶችን ትክክለኛ ገፅታ የማሳየት ስራ የፖለቲካ ሹመኞች ወይም የውጭ ግንኙነት ሙያተኞች ተግባር ብቻ ተደርጎ መወሰድ የለበትም። የተሳካ አፈጻጸም ሊኖር የሚችለው መላው ህዝብ እንደ ሁኔታው የአገሩ አምባሳደር ሆኖ መሳተፍ ሲችል ነው። ይህም የውጭ አገራት ባለሃብቶች በውስጣቸው መተማመን እንዲፈጠር ያደርጋል። ኢንቨስትመንትም እንዲያድግ ያደርጋል።

እርግጥ በአንድ አገር ውስጥ ኢንቨስትመንትን እውን እንዲሆን ሰላም ወሳኝ ጉዳይ ነው። የሰላም ዲፕሎማሲያችንም መሳ ለመሳ መጓዝ አለበት። ስለሆነም በአገር ውስጥ ያለው ሰላም አስተማማኝ መሆኑን ማብሰርና ማሳወቅ የሁሉም ዜጋ ሃላፊነት መሆን ይኖርበታል።

የኢኮኖሚ ዲፕሎማሲው ያስገኘው ውጤት በአጭር ጊዜ ውስጥ ነው። ይህ ጊዘ ደግሞ አገራችን ውስጥ አልፎ አልፎ ብቅ ጥልቅ የሚሉ ግጭቶች በተስተዋሉበት ወቅት ነው። ይህ ሁኔታ ባይፈጠር ደግሞ ምን ያህል ውጤት ሊመዘገብ እንደሚችል ለማወቅ አያዳግትም። ይሁን እንጂ ክንዋኔው በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ሆነንም ቢሆን ዓለም የመሰከረለት ውጤት ማምጣት እየቻልን ነው።

እንደሚታወቀው ሁሉ በአሁኑ ሰዓት እየተከተልን ያለነው ግንኙነት የአገሪቱን ገፅታ ከመለወጡ ባሻገር፤ በአፍሪካ ብቻ ሳይሆን በዓለም አቀፍ መድረኮችም ተሰሚነቷንና ተፅዕኖ ፈጣሪነቷን ከፍ እንዲል ያደረገ ነው።

አገራችን እያካሄደች ያለው ዲፕሎማሲ ስኬት አንዱ ማሳያ ከጎረቤት ሀገሮች ጋር ያለን ሰላማዊ ሁኔታ ነው። ይህ ሁኔታ ከጸብ ይልቅ ሰላምን፣ ከጥርጣሬ ይልቅ አብሮ ማደግን፣ ከመለያየት ይልቅ መደመርን እውን ያደረገ ነው።

ኢትዮጵያ በአጭር ጊዜ ውስጥ ከውጭ አገራት ጋር ያላት ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት እየተጠናከረ መጥቷል። በአሁኑ ሰዓት የውጭ አገራት እየፈጠሩ ያሉት መተማመን የኢትዮጵያ የዲፕሎማሲ ስኬት እየተጠናከረ ለመሆኑ ማሳያ ብቻ ሳይሆኑ፣ በዚያው ልክም የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድና መንግስታቸው በዓለም አቀፉም ይሁን በጎረቤት ሀገሮች ዘንድ ያላቸውን  ተቀባይነትንና አመኔታን በግልፅ የሚያሳዩ ናቸው።

እርግጥ ይህ ተቀባይነት ዝም ብሎ የተገኘ አይደለም። ጠቅላይ ሚኒስትሩና መንግስታቸው ከአራት ወራት በማይዘልቅ ዕድሜ ውስጥ በአገር ቤት ባከናወኗቸው ተግባሮች በዜጎች ውስጥ እየተፈጠረ ያለው የአንድነት ስሜት ነው።

የአገር ውስጥ የቤት ስራዎቻችንን በአንድነትና በኢትዮጵያዊነት ስሜት ማከናወን ከተቻለ፣ የውጭ ግንኙነታችን በዚያው መጠን የሚያድግና ተቀባይነታችንም ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጎለበተ እንደሚሄድ ከላይ በማሳያነት ያቀረብኳቸው አብሮ የመስራትና የተቀባይነት ሁኔታችን እንደሚጨምር ማረጋገጫዎች ናቸው። ይህ የአስተሳሰብ ለውጥ እንዲጠናከር በሁሉም መስኮች በጋራ ተባብሮ መስራት ያስፈልጋል።