በልማት ጎዳና…!

የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ ለማሳደግና የህዝቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ መንግስት የተለያዩ ተግባራትን እያከናወነ ይገኛል፡፡ ልማታዊ መንግስት የተለያዩ ባህሪያት እንዳሉት እሙን ነው፡፡ ከእነዚህም መካከል አንዱና ምናልባትም ዋናው በገበያ ሚኖረው ጣልቃ ገቢነት ነው፡፡ በመጀመሪያዎቹ እድገት ዓመታት መንግስት የተወሰኑ ትላልልቅ ድርጅቶችን በመያዝ መሰረተ ልማትን መዘርጋት የኖርበታል ከዚያም አልፎ መሰረታዊ የህዝብ ጥያቅዎችን ለመመለስ የሚያስችለውን ተግባር መፈጸም ይችል ዘንድ ድርጅቶቹን ይይዛል ያስተዳድራል፡፡

ከዚህ ጎን ለጎን ደግሞ ድርጅቶችን ወደ ግል የማዞሩ ስራ ቀስ በቀስ እያከናወነ ይሄዳል፡፡ በዚህ መልክ ሲጓዝ የነበረው መንግስታችን  አሁን ደግሞ በመንግስት ይተዳደሩ የነበሩትን ትላልልቅ ፕሮጀክቶችን በከፊል ወይም ሙሉ በሙሉ ወደ ግል ለማዛወር ወስኗል፡፡

ይህንን ለማስፈጸም እንዲቻልም ከተለያየ የህብረተሰብ ክፍል የተውጣጣ ኮሚቴ ተሰየሟል፡፡ ይህ ዓይነቱ መንገድ የአገሪቱን ኢኮኖሚ በዘላቂነት ለማሳደግ ብቸኛው አማራጭ ከመሆኑም ባሻገር የልማታዊ መንግስት ባህሪ ነው፡፡

የበርካታ ያደጉ አገራት የዕድገት ሂደት እንደሚያሳየው ለአንድ አገር ምጣኔ ሃብታዊ ፈጣን እድገት  የግሉ የኢኮኖሚ  ዘርፍ የሚኖረው ሚና የጎላ  ነው፡፡ በአሁኑ ወቅት  በኢኮኖሚ  እድገታቸው የዓለም ቁንጮ የሆኑት አገራት ሳየቀር  ኢኮኖሚያቸውን  አሁን የደረሰበት ደረጃ የደረሰው ለግሉ ዘርፍ በተሰጠ ልዩ ትኩረት ምክንያት እንደሆነ እሙን ነው፡፡ ከዚህ በመነሳት ነው የግሉ የኢኮኖሚ ዘርፍ ለሃገራዊ ኢኮኖሚ እድገት ያለው ድርሻ ከፍተኛ ነው የሚባለው፡፡

የግል የኢኮኖሚ ዘርፍ ማደግ የሚችለው ደግሞ መንግስት በተወሰነ ደረጃ ትላልልቅ ፕሮጀክቶችን ለግሉ ዘርፍ አሳልፎ መስጠት የሚያስችለውን አሰራር ተግባራዊ ሲያደርግ ነው፡፡

ለግሉ ዘርፍ አመች ሁንታ ከተፈጠረ የአገር ውስጥም ሆኑ የውጭ ሃገራት ባለሀብቶች በተለያዩ የኢንቨስትመንት ዘርፎች መዋእለ ንዋያቸውን ለማፍሰስ አያመነቱም፡፡  ይህ በሰፊው ሲሆን ደግሞ  ለዜጎች የሥራ እድል መፍጠር ያስችላል፡፡

በተለይ እንደ ኢትዮጵያ በማደግ ላይ ላሉ አገራት የግል የኢኮኖሚ ዘረፉን ለማሳደግ አመች ሁኔታዎችን በመጠር ረገድ የሚከናወኑ ተግባራት ኢኮኖሚውን ከማሳደግ ባሻገር ለኢኮኖሚው መዋቅራዊ ሽግግር አስተማማኝ መሰረት ለመገንባት ያስችላል፡፡

ባለፉት ሁለት አሰርት ዓመታት እየሆነ የመጣው በተወሰነ ደረጃ በመንግስት ተይዘው የተያዙ ድርጅቶችን ወደ ግል የማዞር ተግባር ነበር፡፡ በዚህም መሰረት የተለያዩ ፋብሪካዎቸና ሆቴሎች ከመንግስት ወደ ግል ተዘዋውረዋል፡፡ ምክንያቱም እስካሁን ድረስ በአገራችን የሚታየው የኢኮኖሚ ልማት በተወሰነ ደረጃ መንግስት በኢኮኖሚው እጁን የሚያስገባበት ግን ደግሞ አብዛኛው በሚባል መልክ ለገበያ የሚለቀቅበት ሁኔታ በመሆኑ ነው፡፡

መንግሥት የአገሪቱ ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ ጤናማ በሆነ መልኩ እንዲመራ ሕጋዊ ማዕቀፎችን የማዘጋጀትና አቅጣጫዎችን የማመላከት እንዲሁም የቁጥጥርና የክትትል ተግባራትን ማከናወኑ የተለመደ ቢሆንም በአሁኑ ወቅት ግን ከዚህም ባለፈ መልኩ የመንግስት ድርጅቶችን ሙሉ በሙሉ ወይም በከፊል በአክሲዮን ለመሸጥ እንደሚፈልግ ይፋ አድርጓል፡፡

ይህንን ተከትሎም ጉዳዩን በተገቢው መንገድ የሚመረምርና አዋጭነቱን እያጠና ተግባረዊ እንዲሆን የሚሰራ ኮሚቴ በመንግስት ተቋቁሟል፡፡ ይህ ደግሞ የግሉን ዘርፍ ተሳታፊነትን በማሳደግ  እድገትንና ብልፅግናን ለማፋጠን እንደሰማይ እንደሚያግዝ ሙሁራን ይናገራሉ፡፡

እንደሚታወቀው አገራችን የነፃ ገበያ ኢኮኖሚ ስርዓትን መከተል ከጀመረች ወዲህ የግሉ ዘርፍ ለአገሪቱ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴና እድገት ትልቅ አስተዋፅኦ እያበረከተ ይገኛል፡፡ የሥራ እድል ከመፍጠር ጀምሮ የወጪ ንግድን በማሳደግ መዋቅራዊ ሽግግሩን እውን ለማድረግ የማይናቅ ሚና ተጫውቷል፡፡

ይሁን እንጂ በየጊዜው በሚያጋጥሙ ልዩ ልዩ ችግሮች ምክንያት የግል  ዘርፉ ፈተናዎች አጋተመው መዝለቁ የማይካድ ሃቅ ነው፡፡ በአገሪቱ ያለው ወቅታዊ የምጣኔ ሀብትና የፖለቲካ ሁኔታም ለግሉ የኢኮኖሚ ዘርፍ መስፋፋት የበለጠ አመች ሁኔታን የሚፈጥር ሆኗል፡፡

አሁን መንግስት እየተከተለው ያለው በተለይ  አገሪቱን ያጋጠማት የውጭ ምንዛሬ እጥረት በመፍታት ለግል ኢኮኖሚ ዘርፉ ጉዞ ከባድ ማነቆ የነበረውን ችግር መቅረፍ የሚያስችል ከመሆኑም ባሻገር አገሪቱ ለገጠማት ብድርን የመመለስ አቅም ማነስ ብቸኛ መፍትሄ እንደሚሆን ይታወቃል፡፡

በዋናነት ከሚነሱ ችግሮች መካከል በአገሪቱ አጠቃላይ የኢኮኖሚ እድገትና በግሉ የኢኮኖሚ  ዘርፎች መካከል አለመደጋገፍ ነው፡፡ በኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ውስጥ ያሉት ሁለቱ ዋነኛ ተዋናዮች የግሉና የመንግሥት ዘርፎች ሲሆኑ  የሁለቱ ዘርፎች መደጋገፍ ለአገር ኢኮኖሚ እጅግ አስፈላጊ ቢሆንም እስካሁን በነበሩት በርካታ ዓመታት የነበራቸው መደጋገፍ ዐዚህ ግባ የሚባል አይደለም፡፡

አሁን ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በተለይ ደግሞ ትላልልቅ የመንግስት ድርጅቶችን ወደ ግል ለማዛወር እየተወሰደ ያለው እርምጃ  ዘርፉ  በአገሪቱ ኢኮኖሚ ላይ ያለው ሚና አስተማማኝ ሆኖ እንዲቀጥል  ያስችለዋል ሲሉ ሙሁራን ይተነትናሉ፡፡

ከመሬት አቅርቦት፣ ከፋይናንስ አቅም እንዲሁም ከሕግ ማዕቀፎች ጋር የተያያዙ ችግሮች ባግባቡ በመፍታት  የግሉን ዘርፍ ተወዳዳሪ እንዲሆንና እድገት እንዲያስመዘግብ የሚያስፈልጉትን ግብዓቶች መካከል በመንግሥት በኩል ሊደረግለት የሚገባ ድጋፍ በወቅቱና በሚፈለገው ደረጃ በማድረግና መልካም አስተዳደርንና ፍትሃዊነትን በማስፈን ዘርፉን ውጤታ ማድረግ በሚያስችል መለከ እንቅስቃሴ እየተደረገ ይገኛል፡፡ 

መንግስት አሁን ከጀመረው ለውጥ ጋር በማጣታም ለዘርፉ ማደግ አስፈላጊ ሆኑ ሕጋዊ ማዕቀፎችን ለስራ አመቺ ማድረግ፣ የፋይናንስ አቅርቦትን ማሻሻልና የመሬት አቅርቦትን በማመቻቸት እስካሁን የግል ኢኮኖሚ ዘርፉን ሸብቦ ይዞት የነበረውን ተግዳሮት በመቅረፍ ዘርፉ ውጤታማ ማድረግ የቻላል፡፡

የግሉ ዘርፍ እድገትና ተወዳዳሪነት በአጭር ጊዜ የሚገኝ ለውጥ ተደርጎ መወሰድ የለበትም፡፡ ምርት ለማምረት የሚያጋጥሙ ችግሮችን በዘላቂነት በመፍታት ዘርፉን ማሳደግና ኢኮኖሚውን አስተማማኝ በሆነ መሰረት ላይ መገንባት እንደሚገባም የዘርፉ ባለሙያዎች ይናገራሉ፡፡

ቀደም ሲል  አገሪቱን ያጋጥማት የነበረው የኢኮኖሚ ችግር ቀላል አልነበረም፡፡ የዋጋ ግሽበት፣ የስራ አጥነት፣ የውጭ ምንዛሬ እጥረት እና የእዳ ጫና በዋናነት ከሚጠቀሱት መካከል ጥቂቶቹ ናቸው፡፡ በአገሪቱ ያለው አጠቃላይ የማክሮ ኢኮኖሚው ሁኔታም እየተረጋጋ መሄድ እንዲችል የግሉን  ዘረፍ ማገዝ አማራጭ የሌለው ነው፡፡

የአገሪቱን የብድር ጫና በመቀነስና ያጋጠማት የውጭ ምንዛሪ እጥረት በማቃለል በቀጣይ ዘላቂ መፍትህ ለማረጋገጥ ደግሞ የአምስት ዓመቱ የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ በተገቢው መንገድ እንዲሳካ ተባብሮ መስራት የግድ ይላል፡፡

የፋይናንስ ዘርፉ ለግሉ ዘርፍ እድገት የማይተካ ሚና እንዳለው ያገናዘበ ጥረት  በቀጣይ ማድረግ ጊዜ የማይሰጠው አንገብጋቢ እንደሆነ እሙን ነው፡፡ ለዚህም ነው መንግስት ትላልቅ ሜጋ ፕሮጀክቶች በሙሉ ወይም በከፊል  ለባለሃብቶች ለመሸጥ ማቀዱን በቅርቡ ያስታወቀው፡፡ ከዚሁ ጎን ለጎን ዘርፍ በማሳደግ የአገሪቱን ኢኮኖሚ ለማሻሻል መወሰድ ካለባቸው እርምጃዎች መካከል አንዱ የፋይናንስ ዘርፉን ማሻሻልና ማዘመን ነው፡፡

ቀደም ሲል የተዘረዘሩትን በማስተካከል የግል ኢኮኖሚ ዘርፉ በፍጥነት እንድያድግ በማድረግ በአገሪቱ አጠቃላይ የኢኮኖሚ እድገት ላይ ወሳኝ ለውጥ ማምጣት የቻላል፡፡ ለዚህም ነው መንግስት በአሁኑ ወቅት በመንግስት የተያዙ ድርጅቶችን ወደግል በከፊል ወይም ሙሉ በሙሉ ለማዞር እየሰራ የሚገኘው፡፡