ከጉባኤው ባሻገር

የአፍሪካ-ቻይና የጋራ ትብብር መድረክ ለአህጉሪቱና ለአገራችን ያለው ፋይዳ ጉልህ ነው።  በጉባኤው ላይ አገራችን የአፍሪካ ሚና እንዲጎላ የበኩሏን ሚና ተጫውታለች። ይህም ቻይና ለአፍሪካ የትሰጠውን ድጋፍ በጋራ ተጠቃሚነት መርህ ገቢራዊ እንዲሆን ያስቻለ ነው ማለት ይቻላል።

ከቤጂንጉ የትብብር ፎረሙ ባሻገር፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ ከቻይና መንግስት ጋር በመነጋገርና ስምምነቶችን በመፈራረም ለአገራችን ኢኮኖሚያዊ ጥቅሞችን ማስገኘት ችለዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከተለያዩ አገራት ጋር ያደረጓቸውን የሁለትዮሽ ግንኙነቶችም ስኬታማ ነበሩ።

በተለይ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ በቻይና ቤጂንግ እየተካሄደ ካለው የቻይና አፍሪካ ፎረም ጎን ለጎን ከቻይናው ጠቅላይ ሚኒስትር ሊኪ ኪያንግ ጋር ያደረጉት ውይይት ስኬታማ ነበር። ከውይይቱ በኋላም የሁለቱን አገሮች ግንኙነት የበለጠ የሚያጠናክር ስምምነትቶችንም ተፈራርመዋል። ስምምነቶቹም ሁለቱን አገራት የጋራ ተጠቃሚ የሚያደርጉ ናቸው።

ቻይና በአገራችን ውስጥ የምታደርገው የልማትና የንግድ ስራዎች የስትራቴጂካዊ ግንኙነታች መገለጫ ነው። እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ የሁለቱ አገራት የንግድ ግንኙነት 6 ነጥብ 3 ቢሊየን ዶላር በላይ መድረሱን ሰነዶች ይገልጻሉ።

ይህም የንግድ ልውውጡ በየዓመቱ የ22 በመቶ እድገት እያሳየ መሆኑን የሚያስረዳ ነው። ከዚህ በተጨማሪ ቻይና አፍሪካን ለማግኘት ኢትዮጵያን እንደ ማዕከል እየተጠቀመች መሆኑ የሁለቱን አገራት ግንኙነት ከፍ አድርጎታል።

ምንም እንኳን ሀገራችን ለልማታችን እመርታ በዕድገታችን ላይ አንዲትም ጠጠር ከሚወረውር ማንኛውም ሀገር ጋር መስራት ቢኖርብንም፣ ከልማት ጉዳዩች አንፃር ከቻይና ጋር ያለን ግንኙነት ረብ ያለው ነው፤ በጋራ ጥቅም ላይ የተመሰረተ።

 

እንደሚታወቀው ሁሉ ኢትዮጵያና ቻይና በጋራ የስልጣኔ እሴቶች ላይ የተመሰረተና ረጅም ዕድሜን ያስቆጠረ ታሪካዊ ቁርኝት ያላቸው አላቸው። ሁለቱም ሀገራት ግንኙነታቸውን ሲያስቡ ጥናታዊ ስልጣኔያቸውንና ረጅም የታሪክ ባለቤትነታቸውን ከግምት ውስጥ ባስገባ ሁኔታ ነው።

ይሁንና የዲፕሎማሲ ግንኙነታቸው የተጀመረው እ.ኤ.አ በ1970 መሆኑን መረጃዎች ያመለክታሉ። ታዲያ በእነዚህ ዓመታት ውስጥ በርካታ ፖለቲካል-ኢኮኖሚ ግንኙነቶችን መመስረት ችለዋል።

በዚህም ዛሬ ለደረሱበት በጋራ ጥቅምና መከባበር ላይ ለተመሰረተው፣ አንዱ በሌላኛው አገር የውስጥ ጉዳይ ጣልቃ ለማይገባበትና ሰላማዊ ትብብር ለጎለበተበት ከፍተኛ የሁለትዮሽ ትስስር መሰረት ጥለዋል ማለት ይቻላል።

ቻይና በእነዚህ የሁለትዮሽ ግንኙነት ዓመታት ውስጥ እውነተኛ እና ሊተማመኑባት የሚገባ ሀገር መሆኗን በተግባር አሳይታለች። በተለይም ሀገራችን ለምታደርገው የፀረ-ድህነት ትግል ወሳኝ ሚና ተጫውታለች፤ በመጫወትም ላይ ትገኛለች። ለዚህም ሁለቱ ሀገራት በአሁኑ ወቅት የደረሱበት የግንኙነት ደረጃና ጥንካሬ ህያው ምስክር ነው ማለት ይቻላል።

እንዲሁም ሀገራቱ በከፍተኛ ባለስልጣናት ደረጃ በየጊዜው የሚያደርጉት ግንኙነት እንዲሁም በተለያዩ ጠቃሚ የሁለትዮሽ ጉዳዮች ዙሪያ የሚያደርጉት ውጤታማ ስምምነቶች የግንኙነቱን ጥንካሬና የሁለቱን ሀገራት የተፈላላጊነት ደረጃ የሚያሳዩ ናቸው።

ቻይና ፖታሽን በማልማት፣ የነዳጅ ዘይትን በማውጣት እንዲሁም ልዩ የኢኮኖሚ ዞኖችን በማልማትና በማስተዳደር ረገድ ከሀገራችን ጋር ተባብሮ የመስራት ፍላጎት እንዳለት በተደጋጋሚ በመግለፅ ከአገራችን ጋር እየሰራች ነው።

ይህ ሁኔታም አገራችን የምዕራቡን ዓለም ጋር ብቻ ሳይሆን፣ የምስራቁን ልዕለ-ኃያል የኢኮኖሚ ሀገርንም ጭምር ምን ያህል ቀልብ የሳበች አገር መሆኗን የሚያመላክት ነው። በተለይ ዶክተር አብይ ደ ሃላፊነት ከመጡ በኋላ በሁለቱ አገራት መካከል የተደረጉት ግንኙነቶች የአገራችንን ጥቅም ያስጠበቁ ናቸው።

 

ቻይና ከኢትዮጵያ ጋር በመሰረተ-ልማት፣ በቴክኖሎጂ ሽግግር እና በህዝብ-ለህዝብ ግንኙነቶች በጋራ ለመስራት ስምምነት ላይ ደደርሳለች። ይህም አገሪቱ ሀገራችን ጋር ያላት ትብብር በጋራ ተጠቃሚነት ላይ የተመረኮዘ ነው ማለት ይቻላል።

ባለፉት አመታት የኢትዮ-ቻይና የኢኮኖሚና የንግድ ትብብር ዞኖች መፈጠራቸው፣ አራት የቻይና ኩባንያዎች የኢንዱስትሪ ፓርኮችን ኢትዮጵያ ውስጥ ማቋቋማቸው እና ሌሎች በጋራ ፍላጎት ላይ የተመሰረቱ ጉዳዮች ለጋራ ተጠቃሚነቱ ማሳያ ናቸው።

አገራችን ከቻይና ጋር የምታናውናቸው ተግባራት አገሪቱ የዓለምን ኢኮኖሚ በሁለተኛ ደረጃ የምትመራ ከመሆኑም በላይ፣ በፖለቲካውም ረገድ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተሰሚነት ያላት መሆኑን ነው።

ስለሆነም ኢትዮጵያ ከቻይና ጋር የሚኖራት በጋራ ጥቅም ላይ የተመሰረተ የሁለትዮሽ ግንኙነት የማዕዘን ድንጋይ ነው ማለት ይቻላል። እርግጥ የትኛውም አገር በራሱ የውስጥ ዕምቅ አቅም መተማመንና ይህንንም አጎልብቶ ማደግ ያለበት መሆኑ የሚታወቅ ቢሆንም፤ ከራሱ አቅም ውጭ የሆነን ነገር ከሌሎች ጋር ተባብሮ መስራት ያስፈገዋል። በተለይም አሁን ባለንበት በዘመነ-ሉላዊነት አንድ ሀገር ብቻውን ምንም ሊያደርግ አይችልም።

ዛሬ ለብቻ የሚሮጥበት ዘመን አይደለም። በአሁን ሰዓት ዓለማችን ወደ አንድ ትንሽ መንደርነት በመቀየሯም አንዱ የሌለውን ነገር በቀላሉ ከሌላኛው ማግኘት ስለሚችል የግንኙነቶቹ ጥልቀት ያን ያህል የተሳሰረ መሆኑን የሚያሳይ ነው። ይህ ትስስር ደግሞ በዶክተር አብይ አማካኝነት ጠብቋል። የተሻሉ ጥቅሞቻችንን የምናስከብርበትን አውድ ፈጥረዋል።

ዶክተር አብይ አህመድ ቻይና ለአገራችን የሰጠችን ብድር የክፍያው ጊዜ በ20 ዓመታት እንዲራዘም አድርገዋል። የወለድ ምጣኔውም እንዲቀንስ ስምምነት ላይ ደርሰዋል። ይህ ስምምነታቸው መንግስት ብድሩን በተራዘመ ጊዜ እየከፈለ ያለውን አቅም ህዝብን በሚጠቅሙ የልማት ስራዎች ላይ እንዲያውል ያደርገዋል። እናም ኢትዮጵያ በቤጂንጉ የቻይና አፍሪካ የትብብር ፎረም ጉባኤ ባሻገር ስኬታማ ተግባሮችን በማከናወን አፍሪካዊም ይሁን አገራዊ ተጠቃሚነትን ማረጋገጥ ችላለች።