መድሃኒት የሚቋቋም የወባ በሽታ በደቡብ ምስራቅ ኤሲያ እየተስፋፋ ነው ተባለ

መድሃኒት የሚቋቋም የወባ በሽታ በደቡብ ምስራቅ ኤሲያ እየተስፋፋ መሆኑን የዩናይትድ ኪንግደም እና ታይላንድ ተመራማሪዎች አስታወቁ።
መድሃኒት የሚቋቋመው በሽታ በደቡብ ምስራቅ ኤሲያ በሚገኙት ሃገራት ከካምቦዲያ ወደ ላኦስ፣ ከታይላንድ ወደ ቬይትናም እየተሸጋገረ መሆኑ ተነግሯል።
ተመራማሪዎች እንደሚሉት ከሆነ ለታማሚዎች ተመራጭ የሆነ የወባ መድሃኒት ቢሰጣቸውም ሊሻላቸው አልቻለም።
ከዚህ ግኝት የደረሱት ተመራማሪዎች ይህ በሽታ ወደ አፍሪካ ሊዛመት ይችላል ውጤቱም "እጅግ በጣም አስደንጋጭ" ሊሆን ይችላል ብለዋል።
የወባ በሽታን ለማከም የሚረዳ፣ የሁለት መድሃኒቶች ጥምር ጥቅም ላይ ሲውል ቆይቷል። ይሁን እንጂ ከስድስት ዓመታት በፊት በካምቦዲያ ይህን ጥምር መድሃኒት የሚቋቋም የወባ በሽታ በካምቦዲያ ታይቶ ነበር።
በቅርቡ የተካሄደ ጥናት ግን ይህን መድሃኒቱን መቋቋም የሚችለው የወባ በሽታ ከካምቦዲያ በተጨማሪ በሌሎች የደቡብ ምስራቅ ኤሲያ ሃገራት እንደሚገኝ ይፋ አድርጓል።
ከታማሚዎች የተሰበሰበው የደም ናሙና በአንዳንድ አካባቢዎች በሽታው መድሃኒት የመቋቋም አቅሙ እስከ 80 በመቶ እንደሆነ ያሳያል።
ተመራማሪዎቹ እንደሚሉት ከሆነ አሁንም ቢሆን በሽታውን ለማከም እና ተለዋጭ መድሃኒቶችን ጥቅም ላይ ለማዋል እየሰሩ ይገኛሉ።
የህክምና አገልግሎት በስፋት በማይገኝባቸው የአፍሪካ ሃገራትን ጨምሮ፣ የወባ በሽታን ለመዋጋት ከፍተኛ ሥራ የተከናወነ ቢሆንም፣ መድሃኒት የሚቋቋም የወባ በሽታ ለዘረፉ ፈተና ሆኖ ቆይቷል።
ይህ መድሃኒት የሚቋቋም የወባ በሽታ ወደ አፍሪካ የሚዛመት ከሆነ ከፍተኛ አደጋን የሚደቅን ይሆናል ነው የተባለው። ተመራማሪዎች በሽታውን የምታስተላልፈዋን የወባ ትንኝ ለመቆጣጠር የሚደረጉ ጥረቶች እንዳሉ ሆነው፤ መቀየር ያለበት በበሽታው የተያዙ ሰዎች የሚወስዷቸው መድሃኒቶች ናቸው ይላሉ።
በየዓመቱ 219 ሚሊዮን ሰዎች በወባ በሽታ ይያዛሉ። ከእነዚህም መካከል በብዛት ዕድሜያቸው 5 ዓመት በታች የሆኑ ህጻናትን ጨምሮ 435ሺህ በላይ ሰዎችን ይገድላል። በበሽታው የተያዙ ሰዎች አፋጣኝ ህክምና የማያገኙ ከሆነ፤ የመተንፈስ ችግር እና የሰውነት አካል ስራ ማቆምን ያስከትላል። (ምንጨ፡-ቢቢሲ)