ታንዛኒያ 30 ሚሊዮን ኮንዶሞች ከውጭ አስገባች

በታንዛኒያ ከወራት በፊት የኮንዶም እጥረት እንዳጋጠመ ከተነገረ በኋላ የጤና ጥበቃ ባለስልጣናት እጥረቱን ለማቃለል 30 ሚሊዮን ኮንዶሞችን ወደ አገሪቱ አስገብተዋል።

በርካታ ታንዛኒያዊያን በመንግሥት የሚሰራጨው የኮንዶም አቅርቦት እየቀነሰ በመምጣቱ የኮንዶም መግዣ ዋጋ ላይ እየታየ ያለው ጭማሪ አሳስቧቸዋል።

ዋና ከተማና የቱሪስቶች መናኸሪያ በሆነችው ዳሬሰላም ውሰጥ ሚገኙ አንዳንድ የእንግዳ ማረፊያዎች እርግዝናንና በግብረ ሥጋ ግንኙነት የሚተላለፉ በሽታዎችን ለመከላከል የሚያገለግለውን ኮንዶም ለደንበኞቻቸው ማቅረብ አቁመዋል።

"አንዳንድ መደብሮች እንደ የኮንዶሞቹ አይነት ከአንድ እስከ ሦስት ዶላር በላይ ወጪን ስለሚጠይቁ፤ ይህን ያህል ወጪ አውጥተን ኮንዶም ማቅረብ ስለማንችል አሁን ደንበኞች ራሳቸው ይዘው መምጣት አለባቸው" ሲል አንድ የሆቴል ሰራተኛ ለቢቢሲ ተናግሯል።

የታንዛኒያ ረዳት የጤና ሚኒስትር የሆኑት ዶክተር ፋውስቲን ንዱጉሊል እንደተናገሩት፤ አሁን የሚፈለገው የኮንዶም መጠን ቀርቧል።

"ከ30 ሚሊዮን በላይ ኮንዶሞች አዝዘናል። አሁን የተቀየረው ኮንዶሞቹ የሚሰራጩበት መንገድ ነው፤ ቀደም ባለው ጊዜ ኮንዶሞችን የሚያሰራጩ ተቋማት ነበሩ። አሁን ግን የማሰራጨቱን ኃላፊነት የተሰጣቸው አዳዲስ ተቋማት አሉን።" ያሉት ረዳት ሚኒስትሩ አክለውም "እኛ ማድረግ የፈለግነው አዲሱ አሰራራችን በተገቢው ሁኔታ መስራቱን ማረጋገጥ ነው። በተጨማሪም ግንዛቤ ለመፍጠር እያደረግነው ያለው ዘመቻ ትኩረት ወደ አደረግንባቸው ሰዎች ሲደርስ ኮንዶም እንደተፈለገው ማግኘት ይቻላል" ብለዋል። (ምንጭ፡-ቢቢሲ)