ፌስቡክ በአፍሪካ ላይ አነጣጥረዋል ያላቸውን ገጾችና አንድ የእስራኤል ኩባንያ ማገዱን ይፋ አደረገ

ፌስቡክ በመቶዎች የሚቆጠሩና አፍሪካ ላይ አነጣጥረዋል ያላቸውን ገጾችና አንድ የእስራኤል ኩባንያ ማገዱን ይፋ አድርጓል፡፡

ፌስቡክ ሀሰተኛ ናቸው ያላቸው ገጾች በተለያዩ ሀገሮች ስለሚካሄዱ ምርጫዎችና ስለሌሎችም ፖለቲካዊ ጉዳዮች መረጃ የሚሰራጭባቸው ነበሩ ተብሏል።

ኩባንያው ያስወገዳቸው 265 ገጾች መነሻቸው እስራኤል ሲሆን፤ በሴኔጋል፣ በቶጎ፣ በአንጎላ፣ በኒጀር፣ በቱኒዝያ እንዲሁም በላቲን አሜሪካና ደቡብ ምስራቅ እስያ ላይ ያተኮሩ መረጃዎች ያሰራጩ ነበር።

ፌስቡክ የተሳሳተ መረጃን ከድረ ገጹ አያስወግድም በሚል በተደጋጋሚ ይተቻል። ከአራት ዓመታት በፊት የመረጃ ትክክለኛነት የሚጣራበት አሠራር መጀመሩ ይታወሳል።

ከታገዱ ገጾች ጀርባ ያሉ ግለሰቦች ሀሰተኛ ገጽ በመጠቀም የተሳሳተ መረጃ ይነዙ እንደነበረ ፈስቡክ ባወጣው መግለጫ አትቷል።

በሀሰተኛ ገጾቹ ይሰራጩ የነበሩ መረጃዎች በርካታ የፌስቡክ ተጠቃሚዎች ጋር እንዲደርሱም ተደርጎ ነበር ነው የተባለው።

የፌስቡክ የደህንንት ፓሊሲ ኃላፊ ናትናዬል ግሌይቸር እንደተናገሩት፤ ግለሰቦቹ በተለያዩ ሀገራት የሚሠሩ መገናኛ ብዙሀንን በመምሰል ስለፖለቲከኞች ተደብቀው የነበሩ መረጃዎች "አጋልጠናል" እያሉ እያሰራጩ ነበር።

'አርቺሜድስ ግሩፕ' የተባለ የእስራኤል ተቋም ከነዚህ እንቅስቃሴዎች ጀርባ እንዳለ በምርመራ እንደደረሱበትም ኃላፊው ተናግረዋል።

የፌስቡክ ገጾቹን የፈጠሯቸው ሰዎች እንደ አውሮፓውያኑ ከ2012 እስከ 2019 ለማስታወቂያ ወደ 812 ሺህ ዶላር ገደማ ከፍለዋል። ገንዘቡ የተከፈለው በብራዚል፣ በእስራኤልና በአሜሪካ መገበያያ ገንዘብ ነው።

ኢላማ ከተደጉት ስድስት የአፍሪካ ሀገሮች አምስቱ በ2010 ሀገር አቀፍ ምርጫ ያካሄዱ ሲሆን፤ የቱኒዝያ ምርጫ በሚቀጥለው ዓመት ይካሄዳል።

ፌስቡክ ምርጫ በሚካሄድበት ወቅት የሰዎች ውሳኔ ላይ ተጽዕኖ የሚያሳድሩ የተሰሳቱ መረጃዎችን ባለማገዱ ሲተች ቆይቷል።

(ምንጭ፡- ቢቢሲ)