ሁሌም ሠላም

የአንድ አገር ሠላምና መረጋጋት ዋነኛ ባለቤት ሕዝብ ነው፡፡ የአገሩም ባለቤት እንዲሁ ሕዝብ ነው፡፡ ሠላምና መረጋጋት ለአገር ብልጽግናና ዕድገት ያለው ድርሻም ከሁሉም የገዘፈ ነው። እዚህ ላይ ጥቂት ማሣያዎችን እንጠቃቅስ። ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በመላው ዓለም ሠላምና መረጋጋት የሌላቸው አንዳንድ የዓለም አገሮች የቱን ያህል ለእልቂት ለከፋ ትርምስና ቀውስ እንደበቁ ማየት ተችሏል። በተለይ በመካከለኛው ምሥራቅ ያለውን ሁኔታ ማየቱም በቂ ይሆናል።

የየትኛውም አገር ሠላም በህዝብ ፍላጎት እንጂ በሌላ አይጠበቅም። ስለ ሠላም በሚደረጉ ማናቸውም ክንዋኔዎች ውስጥ የህዝብ ተሳትፎ ፋና ወጊ ነው የሚባለው ያለምክንያት አይደለም። የኢትዮጵያንና የህዝቦቿን ሠላምና መረጋጋት የማይሹ ቡድኖች እየፈጸሙ ያሉት ፀረ ሠላም ድርጊት የት ድረስ እንደ ዘለቀ ዛሬ ከህዝቡ የተሰወረ አይደለም። ህዝብ ሁሌም ከማንኛውም ተግባር በፊት ግራና ቀኝ የሚያይ፣ ህጋዊ አካሄዶችን የሚመረምር፣ የሚያጤን፣ አሉታዊና አዎንታዊ ጎኑን የሚገነዘብ ከዚህም መሠረታዊ ቁም ነገር ተነስቶ  ሚዛናዊ ውሣኔ የሚሰጥ ነው።

የሠላምን ጥቅም ጠንቅቆ የሚረዳ እንደ ኢትዮጵያ ያለ ህዝብ ከቶ አይኖርም ማለት ይቻላል። ለምን ቢባል ይህ ህዝብ ለሠላም እጅግ ከፍተኛ ዋጋ ከፍሏልና ነው። ስለ ሠላም በተቀነቀነ ቁጥር ቀድሞ ከሥፍራው የሚገኘው ያለምክንያት አይደለም። የሠላሙ ባለቤት ሆኖ በመጀመሪያው ረድፍ ላይ የሚቆመውም ለዚሁ ነው።  

አዋጅ ቢወጣ እና ነጋሪት ቢጎሰም ምናልባት ጊዜያዊ መፍትሄ ሊሆን ይችል ካልሆነ በቀር  በዚህ ዘላቂ ሠላምን ከቶ እውን ማድረግ አይቻልም። ለኢትዮጵያ ሠላም መረጋገጥ መሠረቱ ዜጋው ነው። በመሆኑም በኦሮሚያና በኢትዮጵያ ሶማሌ አንዳንድ አካባቢዎች የተፈጠረው ግጭት በአጭር ጊዜ ውስጥ ወደነበረበት ቦታ እንዲመለስ ከተፈለገ መላው ህዝብ ለሠላም ያለውን ፅኑ ፍላጎት መሠረት አድርጎ መስራት ይኖርበታል። በተለያዩ ወቅቶች ህዝቡ የየአካባቢውን ሠላም በመጠበቅ ረገድ ያሳየው ኃላፊነትን በተገቢው የመወጣት እንቅስቃሴ ሁሌም ሊጠቀስ የሚገባው በጎ ተግባሩ ነው። ይህም ተግባር የሠላሙ ባለቤት ህዝቡ ራሱ ስለመሆኑ መልካም አስረጂ ነው።   

ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ በኦሮሚያና በኢትዮጵያ ሶማሌ አንዳንድ አካባቢዎች የተከሰተውን እኩይ ሴራ በፍጥነት በቁጥጥር ሥር ማዋል ይገባል። ይህ ርምጃ ሠላሙን ተነጥቆ ለቆየው ዜጋ ከፍተኛ እፎይታን ይሰጣልና። በተጫረው እሣት አገርና ሕዝብ ለውድመትና እልቂት ይዳረጋሉ።

ትርምስና ሁከት እንዲፈጠር ሆን ብለው የሚጥሩ ቡድኖች ተባባሪዎቻቸውን ብጥብጥና ሁከት እንዲፈጥሩ፣ ሥርዓተ አልበኝነት እንዲሰፍን፣ ሁሉም ነገር ከቁጥጥር ውጭ እንዲወጣ ከፍተኛ ገንዘብ በመመደብ የማተራመስ ተግባራቸውን ሲከውኑ ተስተውለዋል።

እነዚህ ለሠላም ያልቆሙ ቡድኖች አስፈላጊና አመቺ ነው ብለው የሚያምኑበትንና አዋጪ የሚሉትን ግጭትና ሁከት እንዲቀሰቀስ ወይም እንዲገፉበት የሚያስችል ሥልትና ዘዴ ይቀይሳሉ፤ ይጠቀማሉ፡፡ ይህንን ዘዴያቸውንም በሥራ ላይ በማዋል ተጠቅመውበታል፡፡ ብዙውን ጊዜም የወደቁበት ሁኔታ ታይቷል፡፡ ዘለቄታዊ ውጤት ማግኘትም ይሳናቸዋል።

እዚህ ላይ በዋነኛነት መታወቅ ያለበት ቡድኖቹ የሚያካሂዱት የፀረ ሠላም እንቅስቃሴ ለሕዝብ ጥቅምና መብት በመቆርቆር አይደለም፡፡ ይልቁንም የራሳቸውን ሰፊ ጥቅም ለማስቀጠል፣ በዘረፋ ማግኘት ይገባናል ብለው ለሚያስቡት ሀብት ስኬት ለማመቻቸት ነው። ለዚህ ተልዕኮ ሲባል ሰዎችን በመመልመልና በገንዘብ ኃይል፣ በመግዛት ሥምሪት በመስጠት፣ መሣሪያም በማስታጠቅና በማደራጀት የራሳቸውን ጥቅም ለማስከበር ሲፍጨረጨሩም ይስተዋላሉ።

ህዝቡ ደግሞ በማንኛውም መሥፈርት ሠላሙን ተፃርሮ ሊቆም አይችልም። በመሆኑም ለሠላሙ እውን መሆን አጥፊዎችን በማጋለጥ ለህግ ያቀርባል። ለሠላሙ ምን ያህል ቀናዒ እንደሆነም ያሳያል።

ህዝቡ የወደፊት ዕጣ ፈንታው የሚወሰነው አገሪቱን በምትከተለው የመደመር፣ የአንድነትና የፍቅር መስመር መሆኑን ስለሚያውቅ ሁሌም ሠላም ወዳድ ኃይሎች ጋር ይቆማል።  ዜጋው የሠላምን ጠቀሜታ ስለሚገነዘብ ከምንጊዜውም በላይ ሁሌም በየአካባቢው ለሠላሙ  ዘብ እንደቆመ ነው። ህዝቡ በየመንደሩ ላለው የሠላም ሁኔታ ዋነኛ መሠረት ነው። በዚያ አካባቢ ለሚከሰት ማናቸውም የፀረ ሠላም ድርጊት መልሶ የሚጎዳው እርሱን በመሆኑ ለሠላሙ ይበልጥ ይተጋል።

እንዲህ ዓይነቱ ሠላምን የሚያጎሉ፣ ልማትን የሚያፋጥኑና ንትርክን የሚያስቀሩ መንገዶችን መከተል ምርጫው አድርጎ ይሰራል። ይህ ባይቻል ኖሮ፤ ህዝቡ የጀመረውን የፀረ ድህነት ዘመቻ አጠናክሮ ባልቀጠለ ነበር። ከልማት ዕቅዱ በየደረጃው ተጠቃሚ ሆኖ ተፈላጊውን የዕድገት ራዕይ ሰንቆ ባልተጓዘም ነበር። በዚህ ደረጃ ላይ ሆኖ የተጀመረውን ብልጽግናና ዕድገት ለማስቀጠልና በዚያውም ልክ ልማትና ዴሞክራሲው አገር በቀል ፍላጎትን መሠረት ባደረገ መልኩ እንዲጎለብት በብርቱ ይጥራል።

ይህ ህዝብ በአንዳንድ የኦሮሚያና የኢትዮጵያ ሶማሌ አካባቢዎች የአገሪቱን መለወጥ የማይሹ ቡድኖች አማካይነት የተከሰተውን ሁከት ለመቋቋም ህዝቡ በባለቤትነት ስሜት እየከፈለ ያለው መስዋዕትነት በቀላሉ አይታይም። የህዝቡ ስሜት የመነጨው ከቅርብ ወራት ወዲህ በሁሉም መስኮች እየታዩ ካሉት ተስፋዎች በመነጨ ነው።