አንድ እንጨት አይነድም…

በአንድ ሀገር ዘላቂና የተረጋጋ ለውጥ ለማምጣት አንድ የፖለቲካና የኢኮኖሚ ማህበረሰብ መኖሩ ወሳኝ ነው። የህዝቦችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥና ፍትሀዊ የሀብት ክፍፍል እንዲኖር ለማስቻልም ያለው ፋይዳ ጉልህ ነው። ህዝቦች በሀገር ደደህንነት፣ በኢኮኖሚ ዕድገትና በልማት ጉዳዮች ላይ የጋራ መግባባት ሊኖራቸው ይገባል። በዚህም የኢትየዮጵያ ህገ-መንግስት በዋናው ክፍል እንደ አንድ ዓላማ ያስቀመጠው አንድ የፖለቲካ ማህበረሰብን መፍጠር የሚል ነው።   

አንድ የፖለቲካ ማህበረሰብን መፍጠር የሚለውን የህገ-መንግስቱን ዓላማ ለማሳካት ዘርፈ ብዙ ተግባራት ተከናውነዋል ለውጦችም ታይተዋል። ሆኖም ግን የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ በዋነኝነት የተመሰረተው በግብርናው ክፍለ ኢኮኖሚ በመሆኑ በሚፈለገው ደረጃ ውጤት ማስመዝገብ አልተቻለም። አሁን ባለው እንቅስቃሴም ኢኮኖሚውን ለማሻሻል ኢትዮጵያ ከግብርና መር ወደ ኢንዱስትሪ መር የመዋቅር ሽግግር እያደረገች ትገኛለች። ወደ ሁለት አሀዝ አደገ የምንለው የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ከጠቅላላ ዓመታዊ ምርቱ ውስጥ ግማሽ ያህሉ የምርት መጠን ከግብርናው እየተረከበ መሆኑም ይታወቃል።

አሁን ባለው ተጨባጭ ሁኔታ ኢኮኖሚው የግብርናው ክፍለ ኢኮኖሚ ጥገኛ በመሆኑ የግብርናው ዘርፍ ሲጎዳ የኢኮኖሚ እድገቱ መቀነሱ ዋነኛ ማሳያ ነው። ማክሮ ኢኮኖሚው ላይ የሚያደርሰው ተፅዕኖም በቀላሉ የሚታይ አይሆንም። ምክንያቱም  የሀገሪቱ ኢኮኖሚ በግብርናው ላይ የተመሰረተ መሆኑና ግብርናውም ቢሆን ወቅትን ጠብቆ በሚዘንብ ዝናብ ላይ ጥገኛ መሆኑ ነው። 

የኢትዮጵያ ኢኮኖሚያዊ ዕድገት በቀጣይ ለሰላምና ለማህበራዊ መረጋጋት እንዲሁም ለፍትሐዊ የሀብት ክፍፍል ምንጭ መሆን እንዲችል ብዙ ስራዎችን መስራት ይጠይቃል። በተለይም በየጊዜው መጠሪያውንና ባህሪውን እየቀያየረ የሚታየውና የሚሰማውን የዕለት ተዕለት ዝርፊያና ሌብነት ማስቀረት ባይቻልም መቀነስ ይቻላል። ለዚህም ሁሉም ዜጋ ሀላፊነት ሊወስድና መስረቅን አብዝቶ ሊፀየፍ ይገባል።

የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ ከበዓለ ሲመታቸው ዕለት ጀምሮ ባደረጓቸው ንግግሮችና በፈፀሟቸው ታላላቅ ድሎች አንጀቱ ያልራሰ፣ ልቡ በሐሴት ያልዘለለና ያላጨበጨበላቸው ኢትዮጵያዊ የለም። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይዘውት በመጡት አዲስ ለውጥ ከሀገር ቤት ጀምሮ በተለያዩ የዓለም ሀገራት የሚገኙ ኢትዮጵያውያንን “መደመር” በሚል  የሰላም፣ የፍቅርና የአንድነት ፍልስፍና እያስደመሙት ይገኛሉ። አሁን እየታየ ያለው ለውጥ ኢትዮጵያዊነትን ያስቀደመና ሰላምን የሚዘምር ሁለንተናዊ ለውጥ በመሆኑ ከዕለት ዕለት አዳዲስና ያልተጠበቁ ክስተቶች ተስተውለዋል እየተስተዋሉም ይገኛሉ።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ በፓርላማ ዶላርን አስመልክተው የታነቀውን ኢኮኖሚ ለማስተንፈስ በዲፖሲት መልከ ከፍተኛ ቁጥር ያለው ዶላር አስገብተናል። ይህም ጊዜያዊ መፍትሔ ነው። በቀጣይ ዘላቂ የሆነ መፍትሄ ማግኘት የምንችለው በኤክስፖርት የምናገኘውን ግኝት በማሳደግ ስንችል ነው። ኤክስፖርትን ማሳደግ ስንችል ኢኮኖሚው አሁን ባለበት ደረጃ ሳይቆም መቀጠል ይችላል። በማለት ያስተላለፉትን መልዕክት ተከትሎ ለውጦች ታይተዋል።  

በመሆኑም በኢትዮጵያ መደበኛ ያልሆነው የውጭ ምንዛሬ ያለምንም ፖሊሲ ከፍተኛ በሆነ ለውጥ በጣም በፍጥነት መቀነስ ችሏል። ባለፉት ጊዜያት ዶላር ኢትዮጵያ ውስጥ በጣም በከፍተኛ ደረጃ እያሻቀበ ከመሄዱም ባሻገር በሁሉም ባንኮች በሚባል ደረጃ ዶላር ፈላጊዎች በወረፋ ይገበያዩ እንደነበር ይታወቃል። በተለይም በጥቁር ገበያው አንድ የአሜሪካን ዶላር እስከ 38 ብር መመንዘር የተቻለ ቢሆንም አሁን በተነፈሰው የኢኮኖሚ ማነቆ ምክንያት ጥቁር ገበያዎች ከባንክ እኩል አንድ የአሜሪካን ዶላርን በ27 ብር ሊመነዝሩ እንዲሁም ከገበያው ሊወጡም ግድ ሆኖባቸዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ “በግምት ከአንድ ሚሊዮን በላይ ቁጥር ያለው ዲያስፖራ ከቀን ማኪያቶ አንድ ዶላር መስጠት እንደሚችል በመተማመን ለምነዋል። በቀን አንድ ዶላር ማለት ደግሞ በወር 30 ሚሊዮን ዶላር ማግኘት ሲሆን ይህ በመንግስት በጀት አይገባም የራሱ ቦርድ ይቋቋምለታል። በዚህም በበብዙ ቀበሌዎች ከከብት ጋር የደፈረሰ ውሃ የሚጠጡ እናቶች ንፁህ ውሃ ማግኘት ይችላሉ። በመድሃኒትና በአምቡላንስ እጦት ምክንያት የሚሞቱ እናቶች አይሞቱም” ብለዋል።

ይህን ተከትሎም በውጭ ሀገራት የሚገኙ ዲያስፖራዎች ተፈፃሚነቱን በመናፈቅ የተጣለባቸውን ኃላፊነት በከፍተኛ እንቅስቃሴ ለመወጣትና የተጀመረውን ለውጥ ለማቀጣጠል ፍቃደኝነታቸውን ገልፀዋል። ይህም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ባደረጉት የመደመር ጉዞ በአሜረካ ዋሽንግተን ዲሲና በሜኔሶታ ተገኝተው በመደመር ፍልስፍናቸውን አንድነትን፣ ሰላምንና ይቅር ባይነትን ለኢትዮጵያውያን ባስተማሩበት መድረክ ተረጋግጧል። አንድነትን በሚያቀነቅነው በዚሁ ንግግራቸውም ብዙዎች ተደስተዋል፤ የጥላቻ፣ የዘረኝነትና የክፉ ነገሮች ሁሉ ሰንኮፍ ወድቋል።

በሌላ በኩል በቅርቡ በሀገሪቷ እየታየ ያለውን ለውጥ ተከትሎ በርካታ ለቁጥር የሚታክቱና የሚደክሙ ቁጥር ያላቸው የብር ኖቶች፣ የአሜሪካን ዶላሮችና ሌሎቸም የውጭ ሀገር ገንዘቦች እዚህም እዚያም ተያዙ፣ ተገኙና በቁጥጥር ስር ዋሉ እየተባልን ነው። ከዚሁ ጋር ተያይዞ በሀገር ውስጥ የተገኘን ሀብት ወደ ውጭ ማሸሽ አደገኛ አካሄድ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ማሳሰባቸው ይታወሳል። ይህ ተግባርም በሀገሪቱ ላይ ከፍተኛ ኪሳራን የሚያስከትልና የሀገሪቱን ኢንቨስትመንት ወደኋላ የሚጎትት አደገኛ የሙስና መገለጫ መሆኑን ምሁራን ይገልፃሉ።

ህገ-ወጥ የዶላር ምንዛሬን በመከላከልና በመቆጣጠር እየተሰራ ያለው ስራ ይበል የሚያሰኝ ነው። ዳሩ ግን ይህ ስፍር ቁጥር የሌለው ገንዘብ በዚህ ገባ በዚህ ወጣ እየተባለ ከሚነገረው ዜና በተጨማሪ በወንጀሉ የተሳተፉ አካላትን በተመለከተ የሚተላለፍ መረጃ የለም። በህገ-ወጥ መንገድ የሚወጣው ገንዘብስ ለምን ዓላማ እየዋለ ነው?… ይህ ለቁጥር የሚታክት የውጭም ሆነ የሀገር ውስጥ ገንዘብ በተደጋጋሚ እየተያዘ ያለው ከነማን ነው? እንዲሁም ምን አይነት እርምጃስ ተወሰደባቸው?…የሚሉና መሰል ጥያቄዎችን ህዝቡ በአንክሮ የሚመለከታቸው ጥያቄዎች ናቸው። ስለሆነም ጉዳዩ የህዝብ ነውና ህዝቡ ለነዚህ ጥያቄዎች መልስ ሊያገኝላቸው ይገባል። ይህ ካልሆነ ግን ተአማኒነትን ያሳጣል። ከዚህም በላይ ህዝቡ ወንጀለኞችን ለማስያዝም ሆነ ለማንኛውም ጉዳይ ያለው ተባባሪነት ይቀንሳል። ህዝቡን ያላሳተፈ ማንኛውም እንቅስቃሴ ደግሞ ትርፉ ኪሳራ ነው።

በአጠቃላይ በኢትዮጵያ አሁን ያለውን ለውጥ ተከትሎ የምናስተውላቸው ዘርፈ ብዙ ግራ መጋባቶች አሉ። ኪራይ ሰብሳቢነት፣ ሙሰኝነትና እኔ ብቻ የሚል አስተሳሰብ በጉልህ ተንሰራፍቶ ቤት የሰራበት ግለሰብም ሆነ ተቋም ቀፎው እንደተነካ ንብ ግር እያለ እዚህም እዚያም መናደፍ ጀምሯል። አፍቅሮተ ንዋይ ልባቸውን የደፈነው ስግብግቦች “…በሞትኩት አፈር ልብላ፤ አፈር ልጠጣ” ከሚል ህዝብ ሰርቀው ህዝብን ያለሀጥያቱ ዋጋ ሲያስከፍሉት ኖረዋል። እኛ የተደመርን ኢትዮጵያውያን ግን ከህዝብ መስረቅን ልንፀየፈው ይገባል።

ከዚህም በላይ “አንድ እንጨት አይነድም…” እንዲሉ ጠቅላያችን ባስተማሩን ቀኖና በአንድነት፣ በፍቅር፣ በይቅርታና በመቻቻል ውስጥ ሆነን በጋራ ቤታችን ለጋራ ሰላማችን ዘብ ልንቆም ይገባል። በተለይም በሀገሪቷ የተጀመሩ ትላልቅ ለውጦች በተጀመረው ፍጥነት እንዲገሰግሱና ወደኋላ እንዳይቀለበሱ እያንዳንዳችን የበኩላችንን ጠጠር ልንወረውር ይገባል።

 

የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ በጅቡቲ ጀምረው ሱዳንና ኬንያን በጎበኙበት ወቅት የኢኮኖሚና ሌሎች ሥምምነቶች ማድረጋቸው የሚታወቅ ነው። በተለይም ከጂቡቲ ጋር ቀደም ብሎ የታቀድው የኢኮኖሚ ውህደት ሊፋጠን የሚችልበት ሁኔታ ፈጥሯል። ኢትዮጵያ ከጅቡቲ ጋርም ሆነ ከሌሎቹ የምሥራቅ አፍሪካ ሀገሮች ጥብቅ የኢኮኖሚ ሥምምነት ስትመሰርት ወደ ኢኮኖሚ ውህድት ታመራለች። በዚህም የጋራ የሆነ የፖለቲካ ኢኮኖሚ በመመስረት ሀገራቱ ሠላማዊ የሆነና ጥብቅ ግንኙነት መፍጠር ይችላሉ።