የአሸባሪው ህወሓት ርዝራዥ የትግራይን ህዝብ ሰላማዊ ኑሮ እየረበሸ መሆኑ ተገለጸ

ሰኔ 17/2013 (ዋልታ) – ለህግ ማስከበር ዘመቻው በትግራይ ተሰማርቶ የነበረው የሀገር መከላከያ ሰራዊት ለምርጫው ሰላማዊነት ሲባል ወደሌላ የሀገሪቱ አካባቢዎች መንቀሳቀሱን ተከትሎ የአሸባሪው ህሓሓት ርዝራዥ ሚሊሻዎች ከተደበቁበት ጢሻ በመውጣት ሰላማዊውን የትግራይ ህዝብ ሲያሸብሩ እንደነበር ተገለጸ።

የሀገር መከላከያ ሰራዊት የህዝብ ግንኙነት ዳይሬክተር ኮሎኔል ጌትነት አዳነ ዛሬ በሰጡት መግለጫ እንደገለጹት፣ ሀገራዊ ምርጫውን ተከትሎ ከውጭም ከውስጥም ስጋት ስለነበር ሰራዊቱ በመንግስት ትዕዛዝ መሰረት ከትግራይ ወደ ማዕከል፣ ምስራቅ፣ ምእራብና የደቡብ የኢትዮጵያ ክፍል እንዲንቀሳቀስ ተደርጓል።

ይህን ሁኔታ እንደ መልካም አጋጣሚ በመውሰድ በየጢሻው ተደብቆ የነበረው የአሸባሪው ህወሓት ሚሊሻ ህዝቡን ሲያስገድድና ሰላማዊ እንቅስቃሴውን ሲያስተጓጉል ነበር። መከላከያ ሰራዊቱ በወሰደው እርምጃ ህዝብን ወደ ሰላማዊ ኑሮው መመለስ ተችሏል።

እንደ ዳይሬክተሩ ማብራሪያ፣ የወደሙ መሰረተ ልማቶችን በፍጥነት በመስራት ገበሬው እንዲያርስ፣ ነጋዴው እንዲነግድ፣ ተማሪዎች እንዲማሩ ለማድረግ በርካታ ስራዎች  እንደተሰሩ ገልጸዋል።

ይህ መልሶ የማቋቋም ስራ ተጠናክሮ እንዲቀጥል እየተደረገ ባለበት ወቅት የአሸባሪው ሀይል ህዝቡ ተጠቃሚ እንዳይሆን ፋይዳ ቢሲ ትንኮሳዎችን ከተደበቀበት እየወጣ እየተነኮሰ ይገኛል።

ባለፉት 40 አመታት በአሸባሪው ህወሓት ምክንያት አማራጭ እንዳያገኝ ተደርጐ የቆየው የትግራይ ህዝብ አሁንም ነጻ እንዳይሆን ረፍት እየነሱት ይገኛሉ ብለዋል።

የማህበራዊ አንቂዎች ህዝቡን እረፍት እንዲሰጡትና ወደ ልማት እንዲመለስ እንዲያደርጉ ያሳሰቡት ዳይሬክተሩ፤  አሸባሪው ቡድን ህዝቡን እያሽበረ በዚህ እቀጥላለሁ የሚል ከሆነ ዳግም በተጠናከረ መልኩ የሀይል እርምጃ እንደሚወሰድበት አስታውቀዋል።

ህዝቡን በውሸት በማደናገር አሽንፈናል በማለት ማጭበርበር ዋና ተግባሩ የሆነው ይህ አሸባሪ ቡድን ሰሞኑን የሚነዛው የአውሮፕላን ድብደባም እሱ እንደሚለው ሳይሆን ሰኔ 15 ቀን የሰማእታት ቀንን እናከብራለን በሚል ከተደበቀበት በወጣበት ወቅት በተመረጠ መልኩ በራሱ ላይ ብቻ የተወሰደ እርምጃ ነው ማለታቸውን ኢፕድ ዘግቧል።