የኢትዮጵያ መንግስት በትግራይ ክልል የተኩስ አቁም ማወጁ ትክክለኛ እርምጃ ነው – የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር 

ሰኔ 23/2013 (ዋልታ) – የኢትዮጵያ መንግስት በትግራይ ክልል የተኩስ አቁም ማወጁ ትክክለኛ እርምጃ መሆኑን የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር ሙሳ ፋኪ መሀማት ገለጹ።

የኮሚሽኑ ሊቀ መንበር ኢትዮጵያ የወሰደችው ሰብአዊነትን ቅድሚያ የሰጠ የተኩስ ማቆም እርምጃ በህብረቱ ተቀባይነት ያለው እና ግጭቱን ለመፍታትም ትክክለኛ እርምጃ መሆኑን አስታውቀዋል።

የኢትዮጵያ መንግስት በትግራይ ክልል አስተማማኝ ሰላም እንዲሰፍን ሁሉን አቀፍ እና አካታች ዘላቂ የተኩስ አቁም ስምምነት እንዲያደረጉና ለዘላቂ ሰላም ምቹ ሁኔታ እንዲፈጥሩም ህብረቱ ጥሪ አቅርቧል።

ሁሉም ባለድርሻ አካላት በጠላትነት መፈላለግ እንዲያቆሙና የዓለም አቀፍ ህግን መሰረት በማድረግ ለንፁኃን ዜጎች ጥበቃ እንዲያደርጉ፣ በግጭቱ ለተጎዱ ሰዎች ሰብዓዊ እርዳታዎችን ለማድረስም አስቻይ ሁኔታዎችን እንዲፈጥሩ ሊቀመንበሩ ጠይቀዋል።

በትግራይ ክልል ያለውን ግጭት ለመፍታት ትክክለኛው መፍትሄ ፖለቲካዊ ነው ያሉት ሊቀመንበሩ፣ ችግሩን ለመፍታትም ኢትዮጵያን ሰላምና መረጋጋት የሰፈነባት ሀገር ለማድረግ  የምታደርገውን ጥረት ህብረቱ እንደሚደግፍ አስታውቋል።