ሚኒስቴሩ ከተጠሪ ተቋማት ጋር በመሆን የክረምት በጎ አድራጎት መርኃግብርን የአቅመ ደካማ ቤቶችን በማደስ ጀመረ

ሐምሌ 04/2013 (ዋልታ) – የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር እና ተጠሪ ተቋማት የክረምት በጎ አድራጎት መርኃግብር ስራን በዛሬው እለት በአራዳ ክፍለ ከተማ የአቅመ ደካሞችን ቤት በማደስ ጀምረዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ ያስጀመሩት የበጎ ፍቃድ አግለግሎት ስራ አካል የሆነው የአቅመ ደካሞች ቤት እድሳት “በጎ ፍቃደኝነት ለመደጋገፍና ለመግባባት” በሚል እየተከናወነ ነው።

የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴርና ተጠሪ ተቋማት የዘርፉን የአቅመ ደካሞችን ቤት እድሳት በጎ አድራጎት ስራ በአራዳ ክፍለ ከተማ የጀመረ ሲሆን፣ በበጎ ፍቃድ ስራው 13 የአቅመ ደካማ ቤቶችን በአንድ ሳምንት ጊዜ ውስጥ አድሰው ያስረክባሉ ተብሏል።

የኢኖሼሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ አህመዲን መሀመድ (ዶ/ር) መደጋገፍ አንዱ የኢትዮጵያዊነት ባህላችን በመሆኑ ቤቶቹን በማደስ ለወገኖቻችን ያለንን አጋርነት እናሳያለን ብለዋል።

ዘርፉ በተለያዩ ቦታዎች የበጎ ፍቃድ አገልግሎት በመስጠት ልምድ ያላቸው ሰራተኞች ስላሉት ቤቶቹን በአንድ ሳምንት ጊዜ ውስጥ አድሶ ለማስረከብ አቅም እንዳለም ገልፀዋል።

በምርጫ ክልሉ ተወዳዳሪ የነበሩት የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ያኒያ ሰኢድመኪይ (ዶ/ር) ቃል የገቡትን እንደሚፈፅሙ ለወረዳው ነዋሪዎች አረጋግጠዋል።

የአራዳ ክፍለ ከተማ ስራ አስፈፃሚ ሃና የሺንጉስ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር “ከቢሮ ወደ ማህበረሰብ” በሚል ትምህርት ቤቶችን እያገዘ መሆኑን ጠቅሰው ምስጋና ማቅረባቸውን ከሚኒስቴሩ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።