መከላከያ ሰራዊት ትዕዛዝ ሲሰጠው አስፈላጊውን እርምጃ መውሰድ በሚያስችል ቁመና ላይ ነው- ኮሎኔል ጌትነት አዳነ

ኮሎኔል ጌትነት አዳነ

ሐምሌ 07/2013 (ዋልታ) – መከላከያ ሰራዊት ትዕዛዝ በሚደርሰው ጊዜ አስፈላጊውን እርምጃ ሊወስድ በሚያስችል ቁመና ላይ እንደሚገኝ የመከላከያ ሰራዊት የህዝብ ግንኙነት ዳይሬክተር ኮሎኔል ጌትነት አዳነ አስታወቁ።

የመከላከያ ሰራዊት የህዝብ ግንኙነት ዳይሬክተር ኮሎኔል ጌትነት አዳነ ለአዲስ ዘመን ጋዜጣ እንደገለጹት፣ አንዳንድ አሉባልተኞች ያላወቁት ነገር የተኩስ አቁም እርምጃ በክላሽና በመድፍ ብቻ አይደለም፤ ከቃላት መወራወር መቆጠብን ጭምር ያካተተ ነው።

መቼና ምን ማድረግ እንዳለብንም ጠንቅቀን እናውቃለን ያሉት ኮሎኔል አዳነ፣ መከላከያ ሰራዊት ትዕዛዝ በሚደርሰው ጊዜ አስፈላጊውን እርምጃ ሊወስድ የሚችልበት አቋም ላይ እንዳለ አስታውቀዋል።

ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃን ጭምር በሚያራግቡት ወሬ አንደናገርም ያሉት ኮሎኔል ጌትነት፣ ካወጣነው አዋጅ ጋር የሚጻረር ስራ ላለመስራት ስንል ብዙ ከመናገር ተቆጥበናል ብለዋል።

እንደ ኮሎኔል ጌትነት ገለጻ፣ ሰራዊቱ የት ላይ ምን ማድረግ እንዳለበት እና ምን አይነት እርምጃ መውሰድ እንዳለበት ያውቃል፣ የተዛቡ መረጃዎች በተለቀቁ ቁጥር ምላሽ መስጠቱ አስፈላጊ አይደለም የሚል አቋም ተይዟል።

የተዛቡ መረጃዎች ቢሰራጩም በእነሱ ፕሮፓጋንዳ ልክ ወሬ ባለማብዛት ጨዋነታችንን ማሳየት ይጠበቅብናል ያሉት የህዝብ ግንኙነት ዳይሬክተሩ፣ ችግሮች የሚባባሱ ከሆነ ግን የመንግስትን ውሳኔ ተከትሎ የሚተላለፉ እርምጃዎች ሊኖሩ እንደሚችሉ ጠቁመዋል።