ወቅቱን በውል መረዳት እና ራስን ለራስ ህልውና ማዘጋጀት ይገባል- የአማራ ብልፅግና ፓርቲ

የአማራ ብልፅግና ፓርቲ

ጥቅምት 22/2014 (ዋልታ) ህዝብን እንደ ህዝብ ለማጥፋት አስቦና አቅዶ የተነሳን ሀይል ማሸነፍ የሚቻለው እንደ ህዝብ አንድ ሆኖ በመቆምና በመመከት ብቻ እንደሆነ የአማራ ብልፅግና ፓርቲ አስታውቋል።

የአማራ ብልፅግና ፓርቲ ያወጣው ሙሉ መግለጫ እንደሚከተለው ይቀርባል፦

ወቅቱን በውል መረዳት እና ራስን ለራስ ህልውና ማዘጋጀት ይገባል!

አሁን የምንገኝበት ነባራዊ ሀቅ ህዝቦችን በማንነታቸው ለይቶ ለማጥፋት አቅዶ ከተነሳ እና አገርን ለመበታተን ቆርጦ ከተነሳ አሸባሪ ቡድን ጋር  እየተፋለምን የምንገኝበት ወቅት ነው።

ህዝብን እንደ ህዝብ ለማጥፋት አስቦና አቅዶ የተነሳን ሀይል ማሸነፍ የሚቻለው እንደ ህዝብ አንድ ሆኖ በመቆምና በመመከት ብቻ ነው።

ጠላት ከመሳሪያው በላይ አሻግሮ የሚተኩሰው ምላሱ ካሸበረን አንድ ሆነን መቆም አንችልም፤ ህልውናችንን ለማቆየት አስቸጋሪ ሁኔታም መፈጠሩ አይቀሬ ይሆናል።

በመሆኑም ጠላት በግንባር እየደረሰበት ያለውን ሽንፈት በሀሰት ፕሮፖጋንዳ ለማካካስና የጦሩን ስነ ልቦና ለመገንባትና ለወገን ጦር ደጀን የሆነውን ህዝብ ለማደናገር  የሚጠቀምበት ታክቲክ መሆኑን በውል በመረዳት ወቅቱን የሚመጥን ስነ-ልቦና መገንባት ይኖርብናል።

ወቅቱ የህልውና ጦርነት እየተካሄደበት ያለ ወቅት በመሆኑ  በህልውና ዘመቻው የክልሉ መንግስት ያስተላለፈውን ጥሪ በመቀበል  ለራስ ህልውና መቆየት ራስን አዘጋጅቶ እና ተደራጅቶ ጠላት በመጣበት አግባብ ምላሽ መስጠት  ያስፈልጋል።

ይህን ለማድረግ በየደረጃው ከሚገኘው አመራር ጋር ተቀናጅቶና ተናቦ መስራት የሀሰት ፕሮፖጋንዳ  ሆን ብለውም ሆነ ባለማወቅ የሚነዙትን በጥንቃቄ መከታተልና መንግስት ባስቀመጠው አቅጣጫ መሰረት እርምጃ መውሰድ, ወጣቱን በስነ ልቦና መገንባትና የመንግስትን ጥሪ ተቀብሎ  የህልውና ዘመቻውን እንዲቀላቀል ማድረግ ይጠበቃል፡፡

የመከላከያና ልዩ ሀይል ምልመላ ስራ ለነገ የማይባል ተግባር መሆኑን በመገንዘብ  አሁን ለገጠመን ችግር ብቻ ሳይሆን የነገንም በማሰብ የፀጥታ ሀይላችንን ማጠናከር በሁሉም አካባቢ ትኩረት ተሰጥቶት ሊሰራ የሚገባው ተቀዳሚ ተግባር መሆን ይኖርበታል።

ጠላት የመጨረሻ እድሉን አሟጦ እየተጠቀመ ያለበት ሰዓት በመሆኑ የጦርነትን ባህሪ መረዳትና  በሀሰት ከሚራገቡ የማህበራዊ ሚዲያ ወሬዎች ራሳችንን በመጠበቅ  ሁሉም እንደ አቅሙ በህልውናው ላይ የመጣን አደጋ ለመቀልበስ ራሱን ማዘጋጀትና  የመኖር ዋስትናውን በራሱ ለማረጋገጥ ቆርጦ መነሳት ይኖርበታል።

በጠላት የሀሰት ወሬ የሚሸነፉ አማራ የለም!

ህዝባዊ ሆኖ የመጣን ጠላት በህዝባዊ አንድነት አናሸንፈዋለን!

ድሉ የኛ ከመሆኑ የሚያግደው አንዳች ሀይል የለም!