ሰልፉ ኢትዮጵያውያን ለየትኛውም ጫና የማይንበረከኩ መሆናቸውን ያሳዩበት ነው – የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት

ጥቅምት 30/2014 (ዋልታ) – በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች የተካሄዱ ሰላማዊ ሰልፎች ኢትዮጵያውያን ለየትኛውም የዓለም አቀፍ ጫና የማይንበረከኩ መሆናቸውን ያሳዩበት ነው ሲሉ የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ለገሰ ቱሉ (ዶ/ር) ገለጹ።

ሚኒስትሩ ለገሰ ቱሉ ከሰሞኑ በተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች የተካሄዱ ሰልፎች ኢትዮጵያውያን ለየትኛውም የዓለም አቀፍ ጫና የማይንበረከኩ መሆናቸውን ያሳዩ ናቸው ብለዋል።

ሰሞኑን የተካሄዱት ሰልፎች አሸባሪዎችን የትህነግ እና ሸኔ ቡድኖችን የጥፋት ተግባር እንዲሁም የውጭ ሚዲያዎች የተዛባ ዘገባን የሚያወግዙ መሆናቸውን አንስተዋል።

ወራሪው የትህነግ ቡድን ከመደበኛ የጦርነት ሥርዓት ውጪ ውጊያን በማዛነፍ በተለይም በአማራና በአፋር ክልሎች በርካታ ቦታዎች ላይ ወረራ በመፈፀም ከፍተኛ ቁጥር ያለው የሰው ሕይወት በመቅጠፍ፣ የመንግሥትና የግለሰብ ሀብቶችን በመዝረፍና በማውደም ላይ እንደሚገኝ ሚኒስትሩ ለኢፕድ ተናግረዋል።

ይህን አስነዋሪ ድርጊት መመከት የሚቻለው በተቀናጀ የሕዝብ ንቅናቄ በመሆኑ የፌዴራልና የክልል መንግሥታት ባቀረቡት የጋራ የክተት ጥሪ መሠረት ከሕዝቡ በርካታ አዎንታዊ ምላሾች ተሰጥቷል ብለዋል።

ከሰሞኑ በአገሪቱ ከዳር እስከዳር የታየው አሸባሪ ቡድኑንና የውጪ ሚዲያ ጣልቃ ገብነትን የሚያወግዝ ሰላማዊ ሰልፍም በጥሪው የተገኘ ውጤት መሆኑን እንዲሁም ሕዝቡም ለዚህ የህልውና ማስከበሪያ ጥሪ ምላሽ የሰጠበት እንደሆነ አመላካች መሆኑን ጠቅሰዋል።