የሚኒስቴር መስሪያ ቤቶች የ9 ወር የበጀት ዕቅድ አፈጻጸም ግምገማ እየቀረበ ነው

ሚያዝያ 7/2014 (ዋልታ) የፌዴራል መንግሥት ሚኒስቴር መስሪያ ቤቶች ያለፉትን 9 ወራት የበጀት አፈጻጸም ግምገማቸውን እያቀረቡ ይገኛሉ፡፡

የፕላን እና ልማት ሚኒስቴር የክትትልና ግምገማ ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ  ጥሩማር አባተ በሚመሩት የበጀት ግምገማ አፈጻጸም የተለያዩ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቶች የአፈጻጸም ግምገማ አቅርበዋል፡፡

የንግድና ቀጠናዊ ትስስር ሚኒስቴር ባቀረበው የ9 ወር አፈጻጸም ግምገማ የኢትዮጵያን ምርቶች በዓለም ገበያ እንዲተዋወቁ በማድረግ፣ በዓለም የንግድ ድርጅት አባልነት ስምምነቶች ሂደት ደረጃ በተመለከተ እንዲሁም የመሰረታዊ ፍጆታ ዕቃዎች አቅርቦትና ስርጭት በተመለከተ እና ሌሎችም ጉዳዮች ተነስተዋል፡፡

በሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ የትራንስፖርትና ሎጀስቲክ ዘርፉን የማዘመን እና የተቀላጠፈ አገልግሎት ለህዝብ ተደራሽ ማድረግ፣ የብዙኃን የትራንስፖርት ማጓጓዣ ድርሻን ከ34 በመቶ ወደ 37 በመቶ ያደገ መሆኑንና ከሎጀስቲክ ዘርፍ ጠቅላላ የወጪ ንግድ በ68 በመቶ ማደጉ የሚኒስቴሩ ጠንካራ አፈፃፀም መሆናቸው ተጠቅሷል፡፡

በአንጻሩ የውጪ ምንዛሬ እጥረት እና የጸጥታ ችግር ለሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ፈተና ሆኖ ማለፉ ተመላክቷል፡፡

የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን በበኩሉ፥ በ9 ወር የበጀት አፈጻጸም ግምገማው የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት ፍሰት በ2013 የእቅድ ዘመን ከነበረበት 3 ነጥብ 97 ቢሊየን የአሜሪካ ዶላር በመነሳት በ2014 በጀት ዓመት 5 ነጥብ 13 ቢሊየን ወይም 23 በመቶ እድገት ማሳየቱን ገልጿል፡፡

አዳዲስ የኢንቨስትመንት ፍቃድ በመስጠት እና የስራ እድልን በተመለከተ በሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ችግሮች መስተዋላቸውንም ከፕላንና ልማት ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ አመላክቷል፡፡