በሰላም ማስከበር ተልዕኮ ተሠማርተው ወደ ሀገር ቤት ያልተመለሱ የሠራዊት አባላት መኖራቸው ተገለጸ

ሚያዝያ 19/2014 (ዋልታ) በዓለም ዐቀፍ የሰላም ማስከበር ተልዕኮ ተሠማርተው ወደ ሀገራቸው ያልተመለሱ የሠራዊት አባላትን አሰመልክቶ የኢፌዴሪ መከላከያ ሚኒስቴር መግለጫ ሰጠ፡፡

ከሰሜን ዕዝ ጥቃት በፊት ወደ ውጭ ሀገር ሰላም ለማስከበር የተላኩ ትግርኛ ተናጋሪዎች  በሰራዊቱ እና በተልዕኮው ላይ ችግር አይፈጥሩም በሚል በሥራቸው እንዲቀጥሉ መደረጉን መግለጫው ያትታል፡፡

“ሕወሓት የትግርኛ ተናጋሪዎች ወደ ሀገራቸው እንዳይመለሱ በውጭ በሚገኙ የወያኔ ቅጥረኞች የሃሰት ፕሮፖጋንዳ በመንዛቱ በአባላቱ ላይ ውዥንብር ፈጥሯል። ሀገር ቤት ከተመለሳችሁ ትታሰራላችሁ የሚል የማስፈራሪያ ውሸት በመንዛትና በዘረኝነት በመቀስቀስ አገራቸውንና ተቋማቸውን ሲያገለግሉ የነበሩ የትግራይ ተወላጅ የሠራዊት አባላትን የማስኮብለል ሥራ ተሰርቷል” ብሏል ሚኒስቴሩ ባወጣው መግለጫ፡፡

“የሠራዊት አባላቱ ተቋማቸውንና ሀገራቸውን ጠልተው ሳይሆን ወያኔ በሰራው አፍራሽ ሥራ ስጋት ገብቷቸው የተወሰኑ ወታደሮች ሰላም ማስከበር በሄዱበት አገር ቀርተዋል፡፡ ወያኔ ጥቂት አፍራሾችን በውስጣቸው በመፍጠር የእኩይ ዓላው አስፈፃሚ አድርጓቸው እንደነበር ይታወቃል፡፡“ ሲልም መግለጫው አክሏል፡፡

ከዚህ ቀደምም በዳርፉር፣ ተልእኮ ላይ ተሰማርተው የነበሩት ወደ አገር ቤት እንዲመለሱ ሲደረግ በተመሳሳይ ውዥንብር ጥቂት ወታደሮች መቅረታቸውንም ሚኒስቴሩ መግለጫ አስታውሷል፡፡

ሱዳን ከሚገኘው ሳምሪ ከተሰኘው የሕወሓት ገዳይ ቡድን ጋር ተቀላቅለው ሲዋጉ የሞቱም እንደነበረ መግለጫው አትቷል፡፡

በዚህ ሁላ የሕወሓት ፕሮፓጋንዳ ሳይታለሉ ሀገርና ተቋማቸው የሰጣቸውን ግዳጅ ፈፅመው ለተመለሱ የትግርኛ ተናጋሪ የሰራዊትን አባላት መከላከያ ሚኒስቴር ምስጋና አቅርቧል፡፡

የመግለጫው ሙሉ ቃል እንደሚከተለው ቀርቧል፡-

በዓለም አቀፍ የሰላም ማስከበር ተልዕኮ ተሠማርተው ወደ ሃገራቸው ያልተመለሱ ጥቂት የሠራዊት አባላትን አሰመልክቶ የተሠጠ ማብራሪያ

አሸባሪው የህወሃት ቡድን የሃገር ሉአላዊነት ምሽግ የሆነውን መከላከያ ሠራዊት በመምታት ለውጡን ቀልብሶ ወደ ስልጣን በመመለስ ኢትዮጵያን መግዛት፤ መግዛት ካልቻለ የራስን ዕድል በራስ መወሰን በሚል ክልሎችን በመገነጣጠል ኢትዮጵያን የማፍረስ ዓላማ ይዞ ጥቅምት 24 ቀን 2013 ዓ.ም በሠሜን ዕዝ ሰራዊታችን ላይ  ጥቃት ከፈተ፡፡ አሸባሪው ቡድን በሠሜን ዕዝ ሰራዊታችን ላይ ጥቃት ከመፈፀሙ አስቀድሞ በመከላከያ ሠራዊት ውስጥ የሚገኙ ትግርኛ ተናጋሪዎችን “ኢንፍልትሬት” በማድረግ ለእኩይ አላማቸው በማዘጋጀት የሠሜን ዕዝ መከላከያ ሠራዊታችን ላይ ጥቃት በመክፈት ሠራዊታችንን ከውስጥና ከውጭ እንዳጠቃ ይታወቃል፡፡

የህግ ማስከበርና የህልውና ዘመቻው ሲጀመር ከመከላከያ ሰራዊታችን ጋር አብረው ሲሰሩ የነበሩ ከወታደር እስከ ከፍተኛ አመራር ያሉ ትግርኛ ተናጋሪዎች ለዘመቻው ስኬትና እርስ በእርስ እንዳንማታ ሲባል ደመወዝና ቀለባቸው ሳይቋረጥ በቤታቸው እንዲቆዩ መደረጉ ይታወቃል፡፡

ከሰሜን ዕዝ ጥቃት በፊት ወደ ውጭ ሀገር ሰላም ለማስከበር የተላኩ ትግርኛ ተናጋሪዎች ግን በሰራዊታችንና በተልዕኮው ላይ ችግር አይፈጥሩም በሚል በስራቸው እንዲቀጥሉ ተደርጓል፡፡ ሆኖም ግን ህወሃት የትግርኛ ተናጋሪዎች ወደ ሀገራቸው እንዳይመለሱ በውጭ በሚገኙ የወያኔ ቅጥረኞች የሃሰት ፕሮፖጋንዳ በመነዛቱ በአባላቱ ላይ ውዥንብር ፈጥሯል።

ሃገር ቤት ከተመለሳችሁ ትታሰራላችሁ የሚል የማስፈራሪያ ውሸት በመንዛትና በዘረኝነት በመቀስቀስ አገራቸውንና ተቋማቸውን ሲያገለግሉ የነበሩ የትግራይ ተወላጅ የሠራዊት አባላትን የማስኮብለል ስራ ተሰርቷል፡፡ የሠራዊት አባላቱ ተቋማቸውንና ሃገራቸውን ጠልተው ሳይሆን ወያኔ በሰራው አፍራሽ ስራ ስጋት ገብቷቸው የተወሰኑ ወታደሮች ሰላም ማስከበር በሄዱበት አገር ቀርተዋል፡፡ ወያኔ ጥቂት አፍራሾችን በውስጣቸው በመፍጠር የእኩይ ዓላው አስፈፀሚ አድርጓቸው እንደነበር ይታወቃል፡፡

ከዚህ ቀደምም በዳርፉር፣ ተልእኮ ላይ ተሰማርተው የነበሩት ወደ አገር ቤት እንዲመለሱ ሲደረግ በተመሳሳይ ውዥንብር ጥቂት ወታደሮች ቀርተዋል፡፡ ሱዳን ከሚገኘው ሳምሪ ተቀላቅለው ሲዋጉ የሞቱም ነበሩ፡፡ ይሁን እንጂ ሁሉንም ጫና ተቋቁመው ሃገርና ተቋማቸው የሰጣቸውን ግዳጅ ፈፅመው ለተመለሱ የትግርኛ ተናጋሪ የሰራዊታችን አባላት ተቋማችን ከፍተኛ ምስጋና ያቀርብላቸዋል።

በህግ ማስከበርና የህልውና ዘመቻው ወቅት በቤታቸው እንዲቆዩ የተደረጉ እና ከሠላም ማስከበር የተመለሡ በሺዎች የሚቆጠሩ የትግርኛ ቋንቋ ተናጋሪ የሠራዊት አባላት እና ሲቪል ሠራተኞች ዛሬም የተቋሙ አባላት ስለሆኑ መብታቸውና ጥቅማጥቅማቸው ይከበራል፡፡ አሁን ያለው ግጭት በማናቸውም አግባብ ከተፈታ ወደ  ሥራቸው ተመልሰው ሃገራቸውን ያገለግላሉ በሚል አቋም እየተሰራ ይገኛል፡፡

አሁንም በሰላም ማስከበር ተልዕኮ ላላችሁ፤ ከሠራዊት ጋር ግዳጅ እየተወጣችሁ ላላችሁና ለጊዜው ከስራ ውጭ ሁናችሁ ነገር ግን ደመወዝና ጥቅማጥቅማችሁ ተጠብቆ ያላችሁ ወታደሮች በወያኔ አፍራሽ ፕሮፖጋንዳ ሳትንበረከኩ አገራችሁን እንድታገለግሉ፤ ቤተሰባችሁን እንዳትበትኑ፤ ጥቅማችሁ እንዳይቋረጥ፤ በክህደት ታሪክ እንዳትመዘገቡ እናሳስባለን፡፡

የኢፌዲሪ መከላከያ ሚኒስቴር