መንግሥት ለትግራይ ክልል የመልሶ ግንባታ ትግበራ ከተመድ ጋር ስምምንት ተፈራረመ

ሐምሌ 5/2014 (ዋልታ) የኢትዮጵያ መንግሥት በትግራይ ክልል ለሚከናወነው የመልሶ ግንባታ ፕሮጀክት ትግበራ ከተመድ የፕሮጀክት አገልግሎት ቢሮ (UNOPS) ጋር የሦስተኛ ወገን የትግበራ ስምምንት በዛሬው ዕለት መፈራረሙን የገንዘብ ሚኒስቴር አስታወቀ።

ፕሮጀክቱ መንግሥት በዓለም ባንክ የገንዘብ ድጋፍ በኢትዮጵያ በጦርነት የተጎዱ ማኅበረሰቦችን መልሶ የማቋቋም ፕሮጀክት በሚል ውጥን በመላው ሀገሪቱ ለማከናወን ያቀደው ፕሮጀክት አካል መሆኑ ተገልጿል።

የፕሮጀክቱ ዓላማዎችም፣ የመሠረታዊ አገልግሎቶችን እና ለአየር ፀባይ ለውጥ የማይበገር የማኅበረሰብ መሠረተ ልማትን መልሶ መገንባት እና ማሻሻል እንዲሁም በኢትዮጵያ በጦርነት የተጎዱ አካባቢዎች ውስጥ የሚገኙ እና የፆታ ጥቃት ለደረሰባቸው ሴቶች የባለብዙ ዘርፍ ምላሽ አገልግሎቶችን ተደራሽነት ማሻሻል ናቸው።

በስምምነቱ መሠረት UNOPS በትግራይ ክልል የመልሶ መገንባት፣ መሠረታዊ አገልግሎቶችን ማሻሻል እና የአየር ንብረት መቋቋም የሚችል ማኅበረሰባዊ መሠረተ ልማት መገንባት ተግባራትን ያከናውናል ተብሏል።

የተመድ የፕሮጀክት አገልግሎት ቢሮ ከመንግሥት ጋር በገባው ስምምነት መሠረት ማኅበራዊ ተቋማትን ይደግፋል፣ ከማኅበረሰቡ ጋር በመምከርም ማኅበረሰቡ ለሚፈልጋቸው አገልግሎቶች ፈጣን ምላሽ የሚያገኝበትን ምቹ ሁኔታ ይፈጥራል ተብሏል።

በግጭት ምክንያት የተጎዱ መሠረታዊ አገልግሎት የሚሰጡ መሠረተ ልማቶች መልሰው አገልግሎት እንዲሰጡ እንደሚሠራም ተገልጿል።

የተመድ የፕሮጀክት አገልግሎት ቢሮ በትግራይ ክልል በሥራ ላይ የሚቆየው አሁን ያለው ሁኔታ እስኪስተካከል እና መንግሥት በክልሉ መደበኛ አገልግሎት መስጠት እስኪጀምር ድረስ እንደሆ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ አስታውቋል።