አሸባሪው ህወሓት በአፋርና አማራ ክልሎች ከ2ሺሕ በላይ ሴቶችና ህጻናት ላይ የአስገድዶ መድፈር ወንጀል መፈጸሙ ተገለጸ

አሸባሪው ህወሓት

መስከረም 10/2015 (ዋልታ) የሕወሓት አሸባሪ ቡድን አባላት በአፋር እና አማራ ክልሎች ውስጥ ከ2ሺህ 200 በላይ ሴቶች እና ህጻናት ላይ አሰቃቂ በሆነ መንገድ በቡድን በመደራጀት አስገድዶ መድፈርና ሌሎች ጥቃቶች መፈጸማቸውን የሚኒስትሮች ግብረር ኃይል የምርመራና ክስ ኮሚቴ አስታወቀ።

የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን እና የተባበሩት መንግስታት የሰብአዊ መብት ከፍተኛ ኮሚሽነር ፅህፈት ቤት የጋራ ምርመራ ውጤቶችን ተከትሎ በኢትዮጵያ መንግስት የተቋቋመው የሚኒስትሮች ግብረር ኃይል የምርመራና ክስ ኮሚቴ በአፋርና አማራ ክልሎች በሚገኙ ዘጠኝ አካባቢዎች የተፈጸሙ ጥፋቶችን የምርመራ ውጤት የመጀመሪያ ምዕራፍ ሪፖርቱን ረቂቅ አውጥቷል።

የአሸባሪ ቡድኑ አባላት በሴቶችና ህጻናት የቡድን አስገድዶ መድፈርን ጨምሮ ሌሎች ጾታዊ ጥቃቶችን ሲፈጽም መቆየቱ የተመላከተ ሲሆን አካል ጉዳተኞች፣በእስር ላይ የሚገኙ እና ከመኖሪያ መንደራቸው የተፈናቀሉ ሴቶች ለአሸባሪ ቡድኑ ጥቃት ሰለባ ናቸው ብሏል።

ቡድኑ በአማራ ክልል ሰሜን ወሎ 706፣ ደቡብ ወሎ 644፣ በደሴ ከተማ 290፣ በሰሜን ሸዋ 186፣ በዋግኅምራ 142፣ ኮምቦልቻ 49፣ ሰሜን ጎንደር 44 ፣ በደቡብ ጎንደር 94፣ በከሚሴ 37 እንዲሁም በአፋር ክልል 20 ሴቶች እና ህጻናት ላይ በአሰቃቂ ሁኔታ የአስገድዶ መድፈር እንደደረሰባቸው ተመልክቷል።

የአስገድዶ መድፈር እና ጾታዊ ጥቃት የተደረገባቸው ሴቶች ኤች አይ ቪን ጨምሮ ለበርካታ ተላላፊ የሆኑ በሽታዎች መዳረጋቸውን እና በደረሰባቸው የሥና ልቦና ጉዳት ሳቢያ ራሳቸውን ለማጥፋት የተገደዱ እንዳሉም መግለጹን ኢዜአ ዘግቧል።
አሸባሪ ቡድኑ ሴቶች እና ህጻናትን ብቻ ሳይሆን ወጣት ወንዶችን ጭምር አሰቃቂ በሆነ ሁኔታ በቡድን በመደራጀት የመድፈር ጥቃት ያደረሰ ሲሆን የጥቃቱ ሰለባ የሆኑ ግለሰቦችን ብቻ ሳይሆን ግለሰቦቹ የወጡበትን ብሔር ሆን ተብሎ ለማዋረድ ተጠቅሞበታል ይላል ሪፖርቱ።
በመሆኑም በቡድኑ አባላት የተፈጸሙት ወንጀሎች በዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብቶች፣ በዓለም አቀፍ የሰብአዊነት ሕጎች እንዲሁም ከሀገሪቱ ሕጎች አንጻር እጅግ አሰቃቂ የሆኑ የመብት ጥሰቶች እና የጾታዊ ጥቃቶች ናቸው ብሏል ሪፖርቱ።