ፕሬዝዳንት ባይደን የአፍሪካ፣ ላቲን አሜሪካና ካሪቢያን ሀገራት በፀጥታው ም/ቤት ቋሚ መቀመጫ ኢንዲሰጣቸው ጠየቁ

ፕሬዝዳንት ጆ ባይደን

መስከረም 12/2015 (ዋልታ) የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ጆ ባይደን የአፍሪካ፣ ላቲን አሜሪካና ካሪቢያን ሀገራት በተባበሩት መንግስታት የፀጥታው ምክር ቤት ቋሚ መቀመጫ ኢንዲሰጣቸው ጠየቁ።

ፕሬዝዳንት ባይደን በኒውዮርክ እየተካሄደ ባለው የተባበሩት መንግስታት 77ኛ ጠቅላላ ጉባዔ ባደረጉት ንግግር ነው ይህንን ጥያቄ ያነሱት።

ባይደን በንግግራቸው የተባበሩት መንግስታት የፀጥታው ምክር ቤት ለዓለም አቀፍ ተግዳሮቶች ምላሽ ለመስጠት የተሻለ ብቃት እንዲኖረው እና ሁሉንም አካታች እንዲሆን ለማድረግ ሪፎርም እንዲደረግበት ጥሪ አቅርበዋል፡፡

የፀጥታው ምክር ቤት አሁን ላይ 5 ቋሚ እና 10 ተለዋዋጭ በድምሩ 15 መቀመጫዎቸ ያሉት ሲሆን ይህ የመቀመጫ ቁጥር እንዲጨምርም ፕሬዝዳንት ባይደን በንግግራቸው ጠይቀዋል።

በአፍሪካ፣ ላቲን አሜሪካና ካሪቢያን ውስጥ የሚገኙ ሀገራት በተባበሩት መንግስታት የፀጥታው ምክር ቤት ቋሚ መቀመጫ እንዲያገኙ የጠየቁት ፕሬዝዳንት ባይደን አሜሪካ ይህንን አቋም ለረጅም ጊዜ ስትደግፍ ቆይታለችም ብለዋል።

በፀጥታው ምክር ቤት ቋሚ መቀመጫ ያላቸው ሀገራት በእነሱ ላይ ወይም በአጋሮቻቸው ላይ የሚተላለፉ ውሳኔዎችን የመሻር መብት አላቸው።

አሜሪካን ጨምሮ በፀጥታው ምክር ቤት ቋሚ መቀመጫ ያላቸው ሀገራት ምክር ቤቱ ተዓማኒነት ያለው እና ውጤታማ ሆኖ እንዲቀጥል ከአቅም በላይ ከሆኑ ያልተለመዱ ሁኔታዎች ውጪ ድምጽን በድምጽ መሻር መብታቸውን ከመጠቀም እንዲቆጠቡም ባይደን አሳስበዋል።

አፍሪካ በተባበሩት መንግስታት የፀጥታው ምክር ቤት ቋሚ መቀመጫ እንዲኖራት ለማስቻል የተለያዩ ዘመቻዎች እየተካሄዱ መሆኑ ይታወሳል።

የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ከዚህ ቀደም ይህንን የአፍሪካ ሀገራት በተባበሩት መንግስታት የጸጥታው ጥበቃ ምክር ቤት ቋሚ መቀመጫ ማግኘት አለባት የሚለውን ሃሳብ መቀላቀላቸውን ይፋ ማድረጋቸው ይታወሳል።

የደቡብ አፍሪካው ፕሬዝዳንት ሲሪል ራማፎዛ እና የሴኔጋሉ አቻቸው ማኪ ሳል አፍሪካ በተባበሩት መንግስታት የጸጥታው ጥበቃ ምክር ቤት ቋሚ ውክልና አለማግኘቷ ፍትሃዊ እንዳልሆነ ማስታወቃቸውም አይዘነጋም።

የቀድሞው የዚምባብዌ ፕሬዝዳንት ሮበርቶ ሙጋቤ አዲስ አበባ በፈረንጆቹ 2016 በተካሄደው 26ኛው የአፍሪካ ህብረት የመሪዎች ጉባኤ ላይ የተባበሩት መንግስታት የጸጥታው ም/ቤት ማሻሻያ እንዲያደርግ መጠየቃቸውንም የአልዐይን ዘገባ አስታውሷል።