የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለሥልጣን የስራ እንቅስቃሴን የመገናኛ ብዙኃን ኃላፊዎች ጎበኙ

የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር መሐመድ እድሪስ

ግንቦት 21/2016 (አዲስ ዋልታ) የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለሥልጣን በህግ የተሰጠዉን ኃላፊነት እና ተግባር ለመወጣት እያደረገ ያለዉን እንቅስቃሴ የህዝብና የንግድ መገናኛ ብዙኃን የስራ ኃላፊዎች ጎብኝተዋል፡፡

በጉብኝቱ ወቅት የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር መሐመድ እድሪስ ባለሥልጣኑ የመገናኛ ብዙኃንን እና የማስታወቂያውን ዘርፍ ለማሳደግና ለማጎልበት የተቋሙን የሰው ሃይል አቅም መገንባት እንዲሁም የቴክኖሎጂ አጠቃቀም ክህሎትን ማሳደግ ላይ ቅድሚያ ሰጥቶ እየሰራ ይገኛል ብለዋል፡፡

የዋልታ ሚዲያና ኮሙኒኬሽን ኮርፖሬት ዋና ስራ አስፈጻሚ መሀመድ ሐሰን

ከቴክኖሎጂ አጠቃቀም አንፃር ከዘርፉ አካላት ጋር የሚኖረውን ግንኙነት በማዘመን ከማህበረሰቡ የሚመጡ ቅሬታ እና ጥቆማዎችን ተቀብሎ የሚመዘግብ እንዲሁም የመጡ ቅሬታና ጥቆማዎችን አይቶና ገምግሞ ፈጣን ምለሽ መስጠት የሚያስችል የኢትዮጵያ ዲጂታል ሚዲያ አስተዳደር ስርዓት የተሰኘ ሲስተም መዘርጋቱን ዋና ዳይሬክተሩ ጨምረው ገልፀዋል፡፡

የጉብኝቱ ተሳታፊ የሆኑ የመገናኛ ብዘኃን ሃላፊዎች በበኩላቸው ባለሥልጣኑ የመገናኛ ብዙኃንን እና የማስታወቂያውን ዘርፍ ለማሳደግ እና ለማጎልበት እያከናወነ ያለዉ በህግና መመሪያ የተመሰረተ የአሰራር ስርዓት እንዲሁም ከመገናኛ ብዙኃን ጋር ያለውን መልካም ትብብር ቀዳሚ ተግባሩ በማድረግ ለዘርፉ እድገት እያበረከተ ያለውን ስራ አድንቀዋል፤ አክለዉም ባለፉት ዓመታት ያከናወናቸዉ የአቅም ግንባታ ስራዎች እና በቴክኖሎጂ የተደገፉ የአሰራር ስርዓቶች ለመገናኛ ብዙኃን ተቋማት እንደ አርዓያ የሚወሰዱ ተግባራት መሆናቸዉን ገልፀዋል፡፡

በጉብኝቱ ወቅት ባለሥልጣኑ የመገናኛ ብዙኃንን የመረጃ ቋት አያያዝ እና የይዘት ክትትል የሚደረግባቸው አሰራሮች፣ ቅሬታና ጥቆማዎችን የሚቀበልበትን እና የሚፈታበትን ሂደት እንዲሁም የሚጠቀማቸው ቴክኖሎጅዎች በመገናኛ ብዙሃን ኃላፊዎች መጎብኘታቸውን ከባለስልጣኑ ያገኘነው መረጃ መለክታል፡፡