ሚኒስቴሩ ግድቦች ባሉባቸው ተፋሰሶች 30ነጥብ6 ሚሊየን ችግኞች መተከላቸውን ገለጸ፡፡

የመስኖና የኃይል ማመንጫ ግድቦች ባሉባቸው ተፋሰሶች 30 ነጥብ 6 ሚሊየን ችግኞች መተከላቸውን የውሃ ፣መስኖና ኤሌክትሪክ ሚኒስቴር ገለጸ ፡፡

የሚኒስቴር መስሪያቤቱ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ብዙነህ ቶልቻ እንዳመለከቱት ፤ ባሳለፍነው ክረምት በተከዜ፣ በግልገል ጊቤ፣ በስምጥ ሸለቆና በጣና በለስ ተፋሰሶች በ5 ሺ 547 ሄክታር ላይ 30 ነጥብ 6 ሚሊየን ችግኞች ተከላ ተከናውነዋል፡፡

ይህም በስነ-ሕይወታዊ መስክ ተራቁተው የነበሩ አከባቢዎች ወደ ነበሩበት እንደሚለሱ ከማድረጉም በላይ የሃይል ማመንጫ ግድቦቹ በደለል እንዳይሞሉ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው አስረድተዋል ፡፡

ባሳለፍነው ዓመት የመስኖና የሃይል ማመንጫ ግድቦች ባሉባቸው ተፋሰሶች በ134 ሺ 759 ሄክታር መሬት ላይ የተለያዩ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ለመስራት ታቅዶ 130 ሺ 446 ሄክታር መሬት ማልማት መቻሉን አስታውቀዋል ፡፡

በተያዘው አዲስ በጀት ዓመትም ስራው ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አመልክተዋል ፡፡