የአማራ ዴሞክራሲያዊ ኃይል ንቅናቄ የሚያካሂደውን የትጥቅ ትግል “በጊዜያዊነት ለማቆም ውሳኔ ላይ ደርሻለሁ” ሲል አስታወቀ።
ንቅናቄው ትናንት ባወጣው መግለጫ፤ ፀረ መንግስት የትጥቅ ትግልም ሆነ በጦር መሳሪያ የሚካሄዱ ጥቃቶችን ሁሉ በጊዜያዊነት ለማቆም ውሳኔ ላይ ደርሷል።
በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ እየተካሄደ ያለውን አንጻራዊ የለውጥ ጅምር ግንዛቤ ውስጥ ማስገባቱን ያመለከተው የንቅናቄው መግለጫ፤ ለብሄራዊ መረጋጋትና ምቹ የፖለቲካ ምህዳር ለመፍጠር ሲባል የተደረገውን አገራዊ ጥሪ መቀበሉን አስታውቋል።
በመሆኑም ንቅናቄው በጦር መሳሪያ ኃይል የሚካሄዱ ማናቸውንም ፀረ – መንግሥት ጥቃቶችን ከመሰንዘር በጊዜያዊነት ማቆሙን ነው ያረጋገጠው።
ንቅናቄው ከኤርትራ ባወጣው መግለጫ፤ በህዝባዊና ብሔራዊ ጉዳዮች ላይ ለመነጋገር የልዑካን ቡድኑን ወደ ኢትዮጵያ ለመላክም ውሳኔ ላይ መድረሱን ጠቁሟል።
እዚህ ውሳኔ ላይ የደረሰው ” የትጥቅ ትግል እንዲያካሂድ ያስገደዱት የአማራ ህዝብ ጥያቄዎች ስለተመለሱ ሳይሆን በአገራችን በሰላም ለመታገል ዕድሎች ይኖራሉ የሚል ተስፋ የሰነቀ በመሆኑ ብቻ ነው” በማለት በመግለጫው አመልክቷል።
ንቅናቄው፤ ከመላ አማራ ሕዝብ ጎን በመሰለፍ በትጥቅና ያለትጥቅ፣ በይፋና በህቡዕ፣ በአገር ህልውና ላይ የተቃጡ አደገኛ የጥፋት ዘመቻዎች እንዲቀለበሱ የራሱን ሚና መጫወቱን አውስቷል።(ኢዜአ)