የህዝብ ተወካዮች ምክርቤት በዛሬው ዕለት ባደረገው አስቸኳይ ስብሰባ የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅትን የሥራ አመራር ቦርድ ሰብሳቢና አባላትን ሹመት አፀደቀ ።
ምክር ቤቱ በዛሬው ዕለት ባካሄደው 3ኛ ዓመት የሥራ ዘመን አስቸኳይ ስብሰባ የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት የሥራ አመራር ቦርድ አባላትን ለመሾም የቀረበውን የውሳኔ ሓሳብ መርምሮ አፀድቋል ።
ምክር ቤቱ ከምህረት ረቂቅ አዋጅ ጎን ለጎን የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅትን እንደገና ለማደራጀት በወጣው አዋጅ ቁጥር 113 /1987 አንቀጽ 7 መሠረት የድርጅቱን የሥራ አመራር ቦርድ አባላትን ሹመት አጽድቋል ።
በተሠጠው ሹመት መሠረትም አቶ ካሳሁን ጎፌ የቦርድ ሰብሳቢ ፣ ወይዘሮ ጀሚላ ሺምብሩ ፣ ወይዘሮ አበበች ሺከታ ፣ አቶ በቀለ ሙለታ ፣ አቶ ዮናስ አስናቀ ፣ አቶ ወንድወሰን አንዱአለም ፣ አቶ ተካ አባዲ እና አቶ ዳንኤል ክብረት የቦርድ አባል በመሆን በምክር ቤቱ ተሹመዋል ።
ሹመት የተሠጣቸው የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት አመራሮችም የተሠጣቸውን ኃላፊነት በተገቢ ሁኔታ ለመወጣት በምክርቤቱ ፊት ቃለመሃላ ፈጽመዋል ።