9ኛው የኦህዴድ ጉባኤ በተለያዩ አጀንዳዎች ላይ ውይይት እያደረገ ይገኛል

9ኛው የኦህዴድ ጉባኤው ዛሬም ቀጥሎ እየተካሄደ ሲሆን በተለያዩ አጀንዳዎች  ላይ ውይይት እየተደረገ  ይገኛል ።

የኦህዴድ ሊቀመንበር  ዶክተር አብይ አህመድ በተለያዩ  አጀንዳዎች ላይ  ለተደረገው ውይይት  ማጠቃሊያ  ሠጥተዋል  ።

ዶክተር  አብይ  እየተካሄደው ባለው ጉባኤ ላይ  እንደገለጹት  የኦህዴድ ሆነ ኦሮሞ  ድል አደረገ የሚባለው  ለኢትዮጵያ አንድነት ግንባታ  ሲሠራ  ነው ብለዋል ።

አሁን በተገኘው ድል ከመኩራራትና እርስ በእርስ ከመጣላትም ለቀጣይ  ድል  መዘጋጅትና  መሥራት እንደሚገባ  ዶክተር  አብይ በጉባኤው  ተናግረዋል ።

የሐሳብ አሸናፊነትና መልካም  ተጽዕኖን መፍጠር የሚቻለው  በጥንታዊ  የገዳ ሥርዓት ደንብ በሚያዘው መሠረት ሁሉንም  የአገሪቱን  ብሔሮች ፣ ብሔረሰቦችና  ሕዝቦችን የምናቅፍ ሲሆን ብቻ ነው ብለዋል ዶክተር አብይ በንግግራቸው ።

ጠላቶቻችን የሚያውጁብንን ጦርነት ለመቋቋም እርስ በእርስ በመደማመጥ አንዱ ሌላውን  በመደገፍ  የተጀመረውን ጉዞ  ማስቀጠል  እንደሚገባ  ዶክተር  አብይ  ተናግረዋል ።

ስትራቴጂካዊ የትግል ስልትና ጠንካራ አደረጃጀት ካለም የሚያጋጥሙ ፈተናዎች ለመቋቋም ያግዛል ብለዋል  ዶክተር አብይ ።

በአገሪቱ  አሁን የተጀመሩት አይነት የዲፕሎማሲያዊ ሥራዎች  ባለፉት  ዓመታት ቢከናወኑ ኖሮም  ኡን እየታየ ያለውን ዓለምን ያስደመመ የዲፕሎማሲ ስኬቶችን  መፍጠር  ይቻልም እንደነበር  ዶክተር አብይ  በቁጭት ተናግረዋል ።

የጉባኤው  ተሳታፊዎች ከመሥመር የመውጣት ፣ መተራረም ላይ  ክፍተት በመስተዋሉና  ይህም ለጉዞው  ቀጣይነት እንቅፋት በመሆኑ ትኩረት ተሠጥቶበት ሊሠራ እንደሚገባ ጠቁመዋል ።

በጉባኤውም  ጠንካራ ወጣት አመራሮች  ወደፊት ለማምጣት  ምርጫዎች  ይካሄዳሉም ተብሏል ።

በጅማ ከተማ  እየተካሄደ ባለው የኦህዴድ 9ኛ ጉባኤ  ለውይይት የቀረቡት  አጀንዳዎች  በሙሉ ተግባራዊ  እንዲደረጉ በሙሉ  ድምጽ ፀድቀዋል  ።   

ጉባኤው በትናንትና ከሰዓት ውሎው የፕሬዚዲየም ኮሚቴ አባላት ምርጫ  አካሄዷል ።

በትናንትናው ዕለት ምርጫውም ዶክተር አብይ አህመድ በኦህዴድ ሊቀመንበርነትና ሥራ አስፈጻሚነት ፣ አቶ ለማ መገርሳ በምክትል ሊቀ መንበርነትና ሥራ አስፈጻሚነት  ፣ ዶክተር ወርቅህ ገበየሁ የኦህዴድ ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባል እና ወይዘሮ አዳነች አቤቤ የኦህዴድ ማእከላዊ ጽህፈት ቤት ሀላፊ በመሆን ተመርጠዋል ።