የሐዋሳ ከተማ ፖሊስ ህብረተሰቡ ስጋት ለመፍጠር በሚደረጉ ሙከራዎች ሳይደናገር አከባቢውን በንቃት እንዲጠብቅ አሳሰበ

በሐዋሳ ከተማ ስጋት ለመፍጠር ሙከራዎች እየተደረጉ በመሆኑ ህብረተሰቡ ተረጋግቶ አከባቢውን በንቃት ሊጠብቅ እንደሚገባ የሀዋሳ ከተማ ፖሊስ መምሪያ አስታወቀ።

በከተማዋ ከሰሞኑ የተፈጠረውን የፀጥታ ስጋት ችግር ለመቅረፍ የከተው የፀጥታ አካላት ከከተማው ነዋሪዎች ጋር በመሆን በቅንጅት እየሰሩ መሆኑን ፖሊስ አክሎ ገልጿል።

የመምሪያው አዛዥ ኮማንደር መስፍን ዴቢሶ በሠጡት መግለጫ፥ በሀዋሳ ከተማ ማንነታቸውና አላማቸው ያልታወቁ አካላት የከተማውን ነዋሪ ላይ ስጋት ለመፍጠር ያልተጨበጠ የስነ-ልቦና ጦርነት ከፍተዋል ብለዋል።

ባለፉት 3 ቀናትም ምሽትን ተገን በማድረግ የተለያዩ ቀለማትን በግለሰቦች በር እና አጥሮች ላይ በመቀባት ነዋሪው ላይ ጥርጣሬን መፍጠሩን ኮማንደር መስፍን ዴቢሶ ተናግረዋል።

ተግባሩም ለውጡን በማደናቀፍ የህዝቦችን በአንድነት የመኖር እሴት ለማፍረስ ሆነ ተብሎ የተደረገ መሆኑን የከተማው ፖሊስ አረጋግጧል ብለዋል።

ቀለም የሚቀቡትን አካላት ፖሊስ በቁጥጥር ስር ለማዋል ከህብረተሰቡ ጋር በቅንጅት እየሰራ መሆኑን ገልፀው፥ ምንም የፀጥታ ስጋት እንዳይኖር ግን የጸጥታው መዋቅር አስፈላጊውን ጥበቃ እያደረገ እንዳለም ነው የገለጹት።

የተቀቡት ቀለሞች ግን ሁሉም ቤቶች ላይ በመደረጉ ብሄር ተኮር ባለመሆናቸው ህብረተሰቡ በዚህ ሆነ ተብሎ የከተማውን ሰላም ለማወክና በቀጣይ የሚካሄደውን የደኢህዴን ጉባኤ ለማደናቀፍ የሚደረግ ጥረትን ሊያወግዝና ሊያጋልጥ እንደሚገባም አሳስበዋል።(ኤፍ.ቢ.ሲ)