የኦብነግ ሠራዊት ትጥቅ ፈቶ ወደ ሃገር ገባ

የኦጋዴን ብሔራዊ ነጻ አውጭ ግንባር (ኦብነግ) ሠራዊት ትጥቅ በመፍታት ወደ ሃገር ውስጥ ገባ።

የግንባሩ ሰራዊት ትናንት ከአስመራ ተነስተው ጅግጅጋ ከተማ ሲገቡም የክልሉ መንግስት ከፍተኛ ባለስልጣናት እና ደጋፊዎቻቸው አቀባበል እንዳደረጉላቸው ከግንባሩ የትዊተር ገጽ ያገኘነው መረጃ ያመላክታል።

ግንባሩ የዛሬ ወር በሰላማዊ መንገድ ለመታገል ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር ስምምነት ላይ መድረሱ የሚታወስ ነው።

በወቅቱ በኢፌዴሪ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዶክተር ወርቅነህ ገበየሁ የተመራ ልዑክ ወደ ኤርትራ በማምራት ከቡድኑ ጋር ባደረገው ድርድር ስምምነት ተደርሷል።

በዚህም ለረጅም አመታት የትጥቅ ትግልን አማራጭ አድርጎ ሲንቀሳቀስ የቆየው ግንባሩ፥ ወደ ሀገር ቤት ተመልሶ በሰላማዊ መንገድ ለመታገል ስምምነት ላይ መድረሱን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ገልፀው ነበር።

የኦጋዴን ብሄራዊ ነፃ አውጭ ግንባር ከስምምነቱ ቀደም ብሎ ልዑኩን ወደ ሀገር መላኩም ይታወሳል።

የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ ያቀረቡትን የሰላም ጥሪ ተከትሎ መቀመጫቸውን በውጭ ሃገር ያደረጉ ሃይሎች የትጥቅ ትግል በማቆም ወደ ሃገር ቤት ገብተዋል።(ኤፍቢሲ)