ጠ/ሚ ዐቢይ አህመድ ለኤርትራ ህዝብና መንግስት የደስታ መልዕክት አስተላለፉ

የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ የኤርትራን 28ኛ ዓመት የነፃነት ቀን በዓልን አስመልክተው ለሀገሪቱ ህዝብና መንግስት የደስታ መልዕክት አስተላልፈዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዓብይ በመልዕክታቸው ለዓመታት ተቋርጦ የነበረው የሁለቱ ሀገራት ግንኙነት በአሁኑ ወቅት የጋራ መተማመንና ፍላጎትን መሰረት በማድረግ በጥሩ ሁኔታ በመቀጠሉ የተሰማቸውን ደስታ ገልፀዋል።

በቀጣይም የሁለቱ እህትማማች ሀገራት ህዝቦች ግንኙነት የጋራ ፍላጎትና ጥቅምን መሰረት በማድረግ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አንስተዋል።

ኢትዮጵያ በቀጠናው የሚከሰቱ ችግሮችን በጋራ ለመፍታት ቁርጠኛ አቋም ያላት መሆኑን የጠቆሙት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ ለኤርትራ ህዝቦች ሰላምና ብልፅግና መመኘታቸውን ከጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።