የእነ አቶ ጌታቸው አሰፋ መዝገብ ተከሳሾች ጉዳያቸው በሌሉበት እንዲታይ ፍርድ ቤት ትዕዛዝ ሰጠ 

የእነ አቶ ጌታቸው አሰፋ መዝገብ ተከሳሾች በአዲስ ዘመን ጋዜጣ ጥሪ ተደርጎላቸው ባለመቅረባቸው ጉዳያቸው በሌሉበት እንዲታይ ፍርድ ቤት ትዕዛዝ ሰጠ 

በእነ አቶ ጌታቸው አሰፋ መዝገብ በአዲስ ዘመን ጋዜጣ ጥሪ የተደረገላቸው አቶ ጌታቸው አሰፋ፣ አፅበሃ ግደይ፣ አሰፋ በላይና ሲሻይ ልዑል በጥሪው መሰረት ባለመቅረባቸው ጉዳያቸው በሌሉበት እንዲታይ የፌዴራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 1ኛ የወንጀል ችሎት ትዕዛዝ ሰጠ፡፡

ከዚህ ቀደም በነበረው ችሎት አቃቤ ሕግ ካሉት ምስክሮች 29ኙ የሕግ ምስክሮች ጥበቃ እንዲደረግላቸው ያቀረበውን አቤቱታ በወቅቱ ችሎቱ ለዳኞች ብቻ ጥበቃ ትዕዛዝ ቢሰጠም ሕጉ ይህን ስለማይፈቅድ ስም ዝርዝሩን ለማቅረብ መቸገሩን አቃቤ ሕግ በችሎቱ ባቀረበው አቤቱታ ገልጿል፡፡

ችሎቱም ጥበቃ የሚደረግላቸው ሰዎች ስም ዝርዝር አቃቤ ሕግ እንዲያቀርብ የተሰጠውን ትዕዛዝ ባለመፈጸሙ እስካሁን ጥበቃ የተደረገለት ምስክር የለም ብሏል፡፡

ከሐምሌ 18/2011ዓ.ም ጀምሮ ምስክሮችን ለመስማት የተያዘው ቀጠሮ እንደተጠበቀው ሆኖ፣ የችሎቱ መደበኛ ሥራ እስከ ሐምሌ 15 የሚቀጥል በመሆኑ፣ ችሎቱ ነሐሴ 7 እና 8ን  ለተጨማሪ የምስክርነት መስሚያ ቀናት ይዟል፡፡

ተይዘው ጉዳያቸው በፍርድቤት እየታየ ያሉት ተከሳሾች በሒሳብ ደብተራቸው ያላቸውን ገንዘብ እና በቁጠባ ያጠራቀሙትን ገንዘብ በእግድ ምክንያት እስካሁን ለማንቀሳቀስ መቸገራቸውን ለችሎቱ አስረድተዋል፡፡

ችሎቱም ገንዘቡ በሌላ መዝገብ ከታገደ በዚህ መዝገብ ጉዳዩ በቀጥታ ባለመኖሩ የሚሰጥ ትዕዛዝ እንደማይኖር ገልጿል፡፡ ስለጉዳዩም ተከሳሾቹ ጠበቆቻቸውን ቢያማክሩ የተሻለ እንደሚሆን ለችሎቱ አስረድተዋል፡፡