ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ የኤርትራ ጉብኝታቸውን አጠናቀው ተመለሱ

ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ በኤርትራ ያደረጉትን የሁለት ቀናት ይፋዊ የስራ ጉብኝት አጠናቀው ተመልሰዋል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትሩ በአስመራ ቆይታቸው ከኤርትራው ፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ ጋር  ተወያይተዋል፡፡

የኤርትራ የማስታወቂያ ሚኒስትት አቶ የማነ ገብረ መስቀል በትዊተር ገፃቸው እንዳሰፈሩት፥ መሪዎቹ በሁለቱ ሀገራት መካከል እየተከናወነ ያለውን ዘላቂ ሰላም የማስፈን ሂደት ማጠናከር በሚቻልበት አግባብ ላይ መክረዋል።

የዛሬ ዓመት ሁለቱ ሀገራት በተፈራረሙት ባለ አምስት ነጥብ የሰላም እና የትብብር ስምምነት መሰረት ሁሉን አቀፍ ትብብር ማድረግ በሚችሉበት ዙሪያም ተወያይተዋል።

መሪዎቹ አወንታዊ ለውጥ እየታየበት ያለውን የሀገራቱን ግንኙነት እና በአፍሪካ ቀንድ ሰላም የማስፈን ጥረትን የበለጠ ለማስፋትም ተስማምተዋል ነው የተባለው።

በጠቅላይ ሚኒስትሩ የተመራው ልዑክ ከፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ ጋር በመሆን በኤርትራ የሚከናወኑ የልማት ፕሮጀክቶችን ጎብኝቷል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ በቆይታቸው በአስመራ ከተማ ችግኝ ተክለዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ ትናንት ነበር የሁለት ቀናት ይፋዊ የስራ ጉብኝት ለማድረግ ወደ አስመራ ያቀኑት።