የኢህአዴግ ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ሲያካሂድ የነበረውን ስብሰባ አጠናቀቀ

የኢህአዴግ ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ሲያካሂድ የነበረውን ስብሰባ የተለያዩ አቅጣጫዎችን በማስቀመጥ አጠናቀቀ።

የስራ አስፈፃሚ ኮሚቴው አባልና በኢህአዴግ ፅህፈት ቤት የፖለቲካ ፓርቲዎችና ሲቪክ ጉዳዮች ሀላፊ አቶ ፍቃዱ ተሰማ ለኢቢሲ እንደተናገሩት፥ ኮሚቴው በወቅታዊ የፖለቲካ ጉዳዮች፣ የድርጅት ስራዎች እና የአመራር ቁመና ላይ ሀላፊነት በተሞላው መንገድ ህዝብና መንግስትን በሚያስቀጥል መልኩ ዝርዝርና ጥልቅ ግምገማዎችን አካሂዷል።

በዚህ ድክመት ነው ያላቸውን በመለየት በዝርዝር መፍትሄዎችን ያስቀመጠው ኮሚቴው፥ ከሀገራዊ ለውጡ ጋር የመጡ በድክመት ያነሳቸውን ዝንባሌዎችን መመልከቱን ነው ያነሱት።

ለውጡ ህዝቡ በሚፈልገው ደረጃ ወደፊት እንዲሄድ ህዝቡና ሀገሪቱ ወደሚፈለገው የከፍታ ደረጃ እንዲደርሱ የሚታትሩ እንዳሉ ሁሉ በለውጡ የቀድሞውን ይዞ የመቆዘም፣ ህዝበኝነት እና ወላዋይነት በአመረራር ደረጃ እንዳሉና ይህም የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች አንድ ሆነው በአንድ አቅጣጫና እና በተመሳሳይ ፍጥነት እንዳይሄዱ ማድረጉን በድክመት እንደገመገመ ገልፀዋል።

በዚህ ላይም የጋራ ስምምነት መደረሱን በመጠቆም ከድርጅት በላይ ኢትዮጵያና ህዝቦቿ መቀጠል እንዳለባቸው በማንሳት ለውጡን በመምራት ሂደት በተሸለ መረጋጋት፣ መደማመጥ እና ሀላፊነት በሚሰማ አግባብ ግምገማውን መካሄዱን ነው አቶ ፍቃዱ የተናገሩት።

በሀገር ደረጃ የሚስተዋለው የብሄር ፅንፈኝነት ለሀገራዊ አንድነት እና ለፌደራላዊትና ዴሞክራሲያዊት ኢትዮጵያ ችግርና ተግዳሮት እንደሆነ በማንሳት መታገል እንደሚገባ ኮሚቴው ተመልክቷል።

ማንነቶች መከበር ያለባቸው ቢሆንም ኢትዮጵያዊ ማንነትን አስታርቆና አቻችሎ ማስኬድ እንደሚገባ መነሳቱንና በማህበራዊ ሚዲያው ከሚንፀባረቁትና አመራሩም ከሚገዛቸው ፅንፈኝነት በመውጣት መታገል እንደሚገባ ዝርዝር ግምገማ ተካሂዷል ብለዋል።

የህግ የበላይነትን ከማስከበር አንፃር ባለፉት ጊዜያቶች ህግና ስርዓትን ለማስከበር የህዝቡ የሰብዓዊ እና ዴሞክራሲያው መብቶች ተገድበው እንደነበር ከዚህም ለመውጣት በህዝቡ ገፊነት ኢህአዴግ ለውጡን እዚህ ደረጃ ማድረሱን ተመልክቷል።

ነገር ግን ህዝቡ ነፃነቱን አጠቃቀም ላይ ክፍተቶች መታየታቸውን በማንሳት ኮሚቴው በነፃነት እና በደህንነት መካከል ሚዛኑ መጠበቅ እንዳለበት በማንሳት ማንኛውም ጥያቄ በሰለጠነ እና በሰከነ መልኩ ለሀገር ያለውን ፋይዳ በመመልት የተሰጠውን መብት መጠቀም እንደሚገባ መገምገሙን ነው አቶ ፍቃዱ ያነሱት።

ከዚህ ውጪ የሚሄዱ ህገውጥ፣ ስርዓት አልበኝነት እና በሀይል ማንኛውንም ለመፈፀም የሚደረጉ ነገሮች ዋጋ የሚያስከፍሉ በመሆናቸው እና ነፃነቱን የሚፈታተኑ በመሆናቸው እነዚህን ክፍተቶች ከህዝቡ ጋር በመሆን በውስጡም ያሉትን ጉድለቶች በማረም የህግ የበላይነትን ሳይደራደር ማስከበር አለበት የሚል ድምዳሜ በግምገማው መደረሱን አስታውቀዋል።

በለውጡ ላይ ያለውን ብዥታ የተመለከተው ኮሚቴው ለውጡ በህዝብ ግፊት ኢህአዴግ በውስጡ በወሰዳቸው እርምጃዎች የመጣ መሆኑን በማስመር ሁሉም በለውጡ ውስጥ ድርሻ እንዳለው ተመልክቷል።

ኮሚቴው በግምገማው የደረሰባቸውን ድምዳሜዎች ያብራሩት አቶ ፍቃዱ፥ አንዱ ድምዳሜ እንድነትን የሚንዱ ነገሮች መታረም እንዳለባቸው የሚመለከተው ነው ብለዋል።

በብሄራዊ ድርጅቶች መካከል በጋራ ያሳለፏቸው መልካም ነገሮች በጋራ የከፈሏቸው መስዋእቶች እና ትግሎች እንዳሉ ያነሱት አቶ ፍቃዱ፥ ዛሬ ላይ አነስተኛ እና ስትራቴጂክ ያለሆኑ ጉዳዮች አይደለም መታየት ያለባቸው ብለዋል።

ይህንንም ታሳቢ በማድረግ ኮሚቴው አንድነትን የሚጎዱ ነገሮችን በግልጽ በመገምገም አንዱ ድርጅት ሌላው ላይ ጣት መቀሰር ሳይሆን ራሱን ከለውጡ አንፃር እንዲመለከት ድምዳሜ ላይ ተደርሷል ብለዋል።

በጋራ በመስማማት ድምዳሜ የተደረሰባቸውን ነገሮችን በሁሉም ደረጃ መተግበር ላይ ክፍተቶች እንዳሉ ኮሚቴው ተመልክቷል።

ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴው የደረሰባቸውን ድምዳሜዎች መሰረት በማድረግም ቀጣይ አቅጣጫዎችን እንዳስቀመጠ አቶ ፍቃዱተናገርዋል።

በሁሉም የሀገሪተ አከባቢዎች የዜጎች የመዘዋወር እና ንብረት የማፍራት ህገ መንግስታዊ መብት መከበር እንዳለበት በመመለክት የደህንነት እና ነፃነት ሚዛን በተጠበቀ መለኩ የህግ የበላይነት እንዲከበር አቅጣጫ አስቀምጧል።

የለውጡ ስራዎች ተቋማዊ እንዲሆኑ ከማድረግ አንፃር የሚያስፈልጉ ህጎች እና ደንቦችን በማውጣት ህዝቡን ባሳተፈ ሁኔታ እንዲተገበሩም የሚል አቅጣጫ ተቀምጧል።

የለውጡን ትክክለኛ ምን ማለት እና ዓላማው ምንድነው በሚለው ላይ ግልፅነት መፍጠር ሌላው አቅጣጫ መሆኑን አንሰተዋል።

መገናኛ ብዙሃን በህዝብ አብሮነትና መቻቻል እንዲሁም አንድነት እና የህግ የበላይነት ላይ እንዲሰሩ ለማስቻልም እንዲሰራ ኮሚቴው አቅጣጫ ማስቀመጡ ነው የተናገሩት።

ቀጣዩ ሀገር አቀፍ ምርጫም ህገመንግስቱ ባስቀመጠው መሰረት 2012 ላይ መካሄዱ አስፈላጊነት ላይ አቋም በመያዝ እንደ ድርጅትም እንደ መንግስትም ዝግጅት እንዲደረግ ነው አቅጣጫ ያስቀመጠው።

በደቡብ ክልል እየተነሱ ባሉት የክልልነት ጥያቄ በተመለከተ ኮሚቴው መምከሩን የተናገሩት አቶ ፍቃዱ፥ ደኢህዴን በክልሉ እየተነሱ ላሉት ጥያቄዎች ሳይንሳዊ መፍትሄ ለመስጠት ያከናወነውን ጥናት ተመልክቷል።

በጥናቱ መሰረት ደኢህዴን ያቀረበውን የክልልነት መዋቅር የኢህአዴግ ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ በአወንታ መመልከቱን እና ለተግባራዊነቱም ድጋፍ ለማድረግ መስማማቱን ገልፀዋል።

ከኢህአዴግ ውህደት አንጻር በሀዋሳው ድርጅታዊ ጉባኤ በተቀመጠው አቅጣጫ መሰረት በተያዘለት ጊዜ እንዲጠናቀቅ የተካሄደ ጥናት አልቆ ውይይት እየተደረገ መሆኑን እና ሁሉም ብሄራዊ ድርጅቶች መክረውበት ለስራ አስፈጻሚ ኮሚቴው እንዲያቀርቡ አቅጣጫ መቀመጡን ተናግረዋል።