የዩኒቨርሲቲ መግቢያ ውጤት ይፋ ሆነ

አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 19/2008(ዋኢማ)-በ2008 የትምህርት ዘመን የዩኒቨርሲቲ መግቢያ የብቃት መመዘኛ ፈተና የወሰዱ ተማሪዎች ወደ ዩኒቨርሲቲ መግቢያ ውጤት ዛሬ ይፋ ሆኗል።

በዚህም መሰረት በመደበኛ እና በማታ በተፈጥሮ ሣይንስ የትምህርት መስክ ፈተና ወስደው ለወንድ 354 እና ከዚያ በላይ ያመጡ ተማሪዎች ለሴት ደግሞ 340 ያመጡ ተማሪዎች ወደ ዩኒቨርሲቲ ይገባሉ።

በማህበራዊ ሳይንስ የትምህርት መስክ በመደበኛ እና በማታ ፈተና የወሰዱ ተማሪዎች ደግሞ ለወንድ 330 እና ከዚያ በላይ እንዲሁም ለሴት 320 እና ከዚያ በላይ የዩኒቨርሲቲ መግቢያ ውጤት ሆኗል።

በተፈጥሮ ሳይንስ የትምህርት ዘርፍ ሁሉም የታዳጊና አረብቶ አደር ሴት ተማሪዎች 335 እና ከዚያ በላይ ያመጡ እንደዚሁም ሁሉም የታዳጊ ክልልና የአርብቶ አደር አካባቢ ወንድ ተማሪዎች ከፍተኛ የትምሀርት ተቋማትን ለመቀላቀል 340 እና ከዚያ በላይ ውጤት ማምጣት ይጠበቅባቸዋል።

በማህበራዊ እና ተፈጥሮ ሳይንስ የትምህርት ዘርፍ ወደ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ለሚቀላቀሉ የግል ተፈታኞች ለወንድ 360 እና ከዚያ በላይ ፣ ለሴት ደግሞ 355 እና ከዚያ በላይ ማምጣት ይጠበቅባቸዋል።

በማህበራዊ ሳይንስ ለታዳጊና የአርብቶ አደር ሴት ተማሪዎች 315 እና ከዚያ በላይ፤ ለወንዶች ደግሞ 320 እና ከዚያ በላይ፤ በተፈጥሮ ሳይንስ ለታዳጊና የአርብቶ አደር ሴት ተማሪዎች ለወንዶች 340 እና ከዚያ በላይ፣ ለሴቶች ደግሞ 335 እና ከዚያ በላይ የዩኒቨርሲቲ መግቢያ መቁረጫ ነጥብ ሆኗል።

መስማት ለተሳናቸው የተፈጥሮ ሳይንስ ተማሪዎች ለሁለቱም ፆታ 297 እና ከዚያ በላይ ሲሆን፥ በማህበራዊ ሳይንስ የትምህርት ዘርፍ ደግሞ ለሁለቱም ጾታ 275 እና ከዚያ በላይ የከፍተኛ ትምህርት መግቢያ ሆኗል።

ሁሉም አይነስውራን (ወንዶችም ሆነ ሴቶች) 200 እና ከዚያ በላይ  ካስመዘገቡ በመንግስት የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ይመደባሉ። 

በግልም ሆነ በመንግስት ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት በማታም ሆነ በቀን እንዲሁም በርቀት ትምህርታቸውን መከታተል የሚፈልጉ ተማሪዎች 295 እና ከዚያ በላይ ውጤት ማምጣት ይጠበቅባቸዋል።

ብሄራዊ ፈተናውን 246 ሺህ 570 ተፈታኞች የወሰዱ ሲሆን ከእነዚህ ውስጥ 50 በመቶዎቹ 350 እና ከዚያ በላይ ውጤት ማስመዝገብ ችለዋል።

106 ተፈታኞች ደግሞ 600 እና ከዚያ በላይ ውጤት ያመጡ ሲሆን ከዚህ ውስጥ 21ዱ ሴቶች ናቸው።

በሌላ በኩል የ10ኛ ክፍል ብሄራዊ ፈተና ውጤት ከሶስት ቀናት በኋላ ይፋ እንደሚሆን የሀገር አቀፍ የትምህርት ምዘናና ፈተናዎች ኤጀንሲ አስታውቋል።(ኤፍ.ቢ.ሲ)