የጉባኤው የበላይ ጠባቂ አባቶች በኢንጂነር ስመኘው በቀለ ህልፈት የተሰማቸውን ጥልቅ ሃዘን ገለጹ

የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ የበላይ ጠባቂ አባቶች  በኢንጂነር  ስመኘው  በቀለ  ድንገተኛ  ህልፈት  ምክንያት  የተሰማቸቸውን  ጥልቅ  ሃዘን ገለጹ ።

በተለያዩ ሰባት ሐይማኖቶች የተውጣጡት የሃይማኖት አባቶቹ በዛሬው ዕለት በጽህፈት ቤታቸው በሠጡት መግለጫ እንደገለጹት  የታላቁ ህዳሴ ግድብ ዋና ሥራ አስኪያጅ በነበሩት ኢንጂነር ስመኘው በቀለ ድንገተኛ ህልፈት  ምክንያት  የተሰማቸውን ጥልቅ ሃዘን ገልጸዋል ።

በተጨማሪም አባቶቹ በአንዳንድ የአገሪቱ አካባቢዎች የተፈጠሩ ግጭቶች ምክንያት ሕይወታቸውን ላጡት ላጡትና ጉዳት  ለደረሰባቸው  ቤተሰቦች  በሙሉ  መጽናናትን  ተመኝተዋል ።

የሃይማኖት  አባቶቹ  በአገሪቱ እየተከሰቱ ያሉት  ግጭቶችን በአጭር ጊዜ  እንዲቆምና ችግሩን ሙሉ ለሙሉ ሊፈታ  እንዲችል  በተጠና  መንገድ  ምላሽ  እንዲሠጠውም ጠይቀዋል  ።

በተለይ  በጉጂና ጌዲኦ አካባቢዎች በተፈጠሩት ግጭቶች  ምክንያት ከመኖሪያ ቤታቸው ተፈናቅለው  በተለያዩ የመጠሊያ ጣቢያዎች  የሚገኙትን  ዜጎች  አስፈላጊው  ሰብዓዊ ድጋፍ እንዲደረግላቸው ያሳሰቡት የሃይማኖት አባቶቹ በልማት ድርጅቶቻቸው አማካኝነት  ለተፈናቃዮቹ  ድጋፍ  እንደሚያደርጉም ገልጸዋል ።     

በአሁኑ ወቅት በመንግሥት በኩል እየተደረገ ያለውን የይቅርታ ፣ የእርቅ ፣ የምህረት፣ የፍቅርና የአንድነት አስተሳሰብ በሃይማኖትም የሚደገፍ በመሆኑ መንግሥት የህግ የበላይነትን  በሚያስከብር  መልኩ ለዜጎች   ሰላም መጠበቅ እንዲሠራ ጥሪ  አቅርበዋል ።

በአገሪቱ  እያገለገሉ  የሚገኙ የሃይማኖት  መሪዎችና አስተማሪዎች በተለያዩ አካባቢዎች ዘርንና  ሃይማኖትን ሽፋን በማድረግ የሚፈጠሩ  ግጭቶችን ወደባሰ  ደረጃ  እንዳይሸጋገሩ የተለመደ  መንፈሳዊ  ኃላፊነታቸውን እንዲወጡም  የሃይማኖት  አባቶቹ  በመግለጫው ጥሪ አቅርበዋል ።