አርቲስት ፍቃዱ ተክለማርያም ትናንት ማምሻውን በ62 አመቱ ከዚህ ዓለም በሞት መለየቱ ተገለጸ።
የብሄራዊ ቴአትር ስራ አስኪያጅ ረዳት ፕሮፌሰር ነብዩ ባዬ እንደተናገሩት ዜና እረፍቱ ትናንት ማምሻውን የተሰማ ሲሆን ዛሬ ወደቦታው አርቲስቶች እንደሚሄዱ ተናግረዋል።
በ1948 ዓ.ም በአዲስ አበባ አራት ኪሎ አካባቢ የተወለደው አርቲስት ፍቃዱ ተክለማርያም የመጀመሪያ ትምህርቱን ሚያዚያ 27 አና አጼ ናዖድ ትምህርት ቤቶች አስከ ዘጠነኛ ክፍል ተምሯል።
በ1967 ዓ.ም በአዲስ አበባ ቲያትርና ባህል አዳራሽ ቅርብ ጓደኛው በነበረው ከሱራፌል ጋሻው ጋር የመቀጠር እድል አጋጠመው::
ፍቃዱ ላለፉት 33 ዓመታት በመድረክ፣ በሬዲዮ፣ በቴሌሺዥን እና አሁን ደግሞ በፊልም በርካታ ሚናዎችን እየወከለ ተጫውቷል፡፡
በአብይነት ከተሳተፈባቸው ወጥና ትርጉም ተውኔቶች መካከል ኦቴሎ፣ ኤዲፐስ ንጉሥ፣ ሐምሌት፣ ቴዎድሮስ፣ ንጉሥ አርማህ፣ መቃብር ቆፋሪውና የሬሣ ሳጥን ሻጩ፣ የሰርጉ ዋዜማ፣ አቡጊዳ ቀይሶ፣ ባለካባ ባለዳባ፣ መልዕክተ ወዛደር እና የመሳሰሉት ይጠቀሳሉ::
ከተወናቸው ተውኔቶች መካከል ያልተከፈለ እዳ፣ ያበቅየለሸ ኑዛዜ፣ ባለጉዳይ እና የመሳሰሉት በህዝብ ዘንድ አድናቆትን ያተረፉለት ስራዎቹ ናቸው፡፡
ከዚህም ሌላ ፍቃዱ “መጽሃፍት ዓለም” ይባል በነበረው የሬዲዮ ፕሮግራም “ሞገደኛው ነውጤ፣ ጥቁር ደም፣ ሳቤላ፣ የነበረው እንዳልነበር” የተባሉትን አጭርና ረጅም ልቦለዶችን ተውኔታዊ መልክ በመስጠት ቀልብን በሚይዝ የአተራረክ ስልት አቅርቧቸዋል፡፡
ፍቃዱ በኋላም እየታወቀ የወጣው ከመድረክ ይልቅ በፊልም ሥራዎች ላይ ነው፡፡ ከተወነባቸው መካከል አንድ በሆነው “ቀይ ስህተት” በተባለው ፊልም የተዋጣለት ፊልም ለመሥራት በመብቃቱ “አቶዝ” በሚል መጠሪያ የምትታወቀውን መኪና የቴዲ ስቱዲዮ እንደሸለመው ይታወሳል።
አርቲስቱ ባደረበት የኩላሊት በሽታ ሳቢያ ውጪ አገር ሄዶ ለመታከም ገንዘብ ቢሰበሰብለትም ከተሰበሰበው ገንዘብ 200 ሺህ ብር ለአንዲት ኩላሊት ታማሚ ሰጥቶ ወደ ፀበል መግባቱ ይታወሳል።(ኢዜአ)