ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ የኢድ አል አደሃ በዓልን በማስመልከት የመልካም ምኞት መግለጫ አስተላለፉ

የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አሕመድ የአረፋና የኢድ አል አደሀ በዓልን በማስመልከት የመልካም ምኞት መግለጫ አስተላልፈዋል።

ከጠቅላይ ሚኒስቴር ጽህፈት ቤት የተላከው የመልካም ምኞት መግለጫ ሙሉ ቃል እንደሚከተለው ቀርቧል።

በሀገር ቤት እና ከሀገር ውጪ የምትገኙ ኢትዮጵያውያን ሙስሊም ወገኖቼ፣ በመላው ዓለም በሚገኙ የእስልምና ሃይማኖት ተከታዮች ዘንድ በታላቅ ድምቀት በየዓመቱ በክብር ለሚነሳው እና ዘንድሮም ለ1ሺህ 439ኛ ዓመተ-ሂጅራ ለሚከበረው የኢድአል አድሃ አረፋ በአል እንኳን በሠላም አደረሳችሁ- አደረሰን!

ኢድ ሙባረክ !

በፆም፣ በፀሎትና ክፉ ምግባርን በሚኮንን ሀይማኖታዊ ሥርዓት የሚከናወነው የአረፋና የሀጅ ሥርዓት ከአምስቱ የእስልምና መሠረታዊ ምሶሶዎች መካከል አንዱ ሲሆን በእስልምና ሃይማኖት ትልቅ ሥፍራ የሚሰጠው ታለቅ በዓል ነው፡፡ በእምነቱ አስተምህሮት በግልጽ እንደተቀመጠው በዙል ሂጃህ ወር ዘጠነኛ ቀን የሚከናወነው የአረፋ ሥርዓት የእስልምና ሃይማኖት የመጨረሻ ከፍታውን ያገኘበት እና የቁርአን የመጨረሻ አንቀፆች ለነቢዩ መሀመድ (ሠዓወ) የወረደበት እለት ከመሆኑም በተጨማሪ በአንድ በኩል አደምና ሀዋ ከጀነት ከወጡ በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ በምድር የተገናኙበትና አወቅኩሽ አወቅሽኝ የተባባሉበትን ድንቅ ተዓምራት ማስታወሻም ጭምር ነው፡፡ ነቢዩላ ኢብራሂም በፈጣሪያቸው ትዕዛዝ አንድ ልጃቸውን እስማኤልን ለመስዋዕት አቅርበው ለፈጣሪያቸው ትዕዛዝ ከመገዛታቸው የተነሳ በልጃቸው ምትክ የበግ መስዋዕትነት የተተካላቸው መሆኑን የምናስታውስበት ዕለት በመሆኑ ለሁላችንም የታዛዥነትን ከፍታ እና የእምነትን ልእልና የሚያጸድል ግሩም በአል ነው፡፡

ውድ የሀገራችን የእስልምና ሃይማኖት ተከታይ ወገኖቼ፣

የዘንድሮውን የአረፋና ኢድ አልአድሃ በዓል ልዩ የሚያደርገው ሀገራችን በአዲስ የለውጥ እርምጃ መጓዝ በጀመረችበት ማግስት የሚከበር መሆኑ ብቻ ሳይሆን ለዓመታት ተከፋፍሎ የቆየው የሙስሊም ማኀበረሰብ አንድነቱን ለማጠናከር በጋራ መንቀሳቀስ በጀመረበት አዲስ የታሪክ ምዕራፍ ላይ ሆነን የምናከብረው መሆኑ በዓሉን ድርብ ድርብርብ የደስታ በአል ያደርገዋል፡፡ የእስልምና እምነት ተከታይ በሆነው ኀብረተሰባችን መካከል የሚፈጠር አንድነት ለሙስሊሙ ወገናችን ብቻ ሳይሆን ለሀገራችንም አንድነትና ጥንካሬ ምንጭ መሆኑን መንግስት አበክሮ ይገነዘባል፡፡ አረፋ በዓልም የመስጠት፣ የደግነትና የቸርነት በዓል በመሆኑ የተቸገሩና አንዳች ጥሪት የሌላቸው ወገኖቻችንን በመርዳት በመልካምና ደግ ሥራ በዓሉን ከተቀረው ወገኖቻችን ጋር በጋራ እንድናከብር ጥሪዬን ላቀርብ እወዳለሁ፡፡

ውድ የሀገራችን ሙስሊሞች፣

በሀገራችን የዘመናት የአብሮነት ታሪክ ውስጥ መቻቻል፣ መተዛዘን እና መረዳዳት ያለውን ፋይዳ በውል የሚረዳው የሀገራችን ሙስሊም ማኀበረሰብ በሠው ልጅ የዘመናት ጥረትና ድካም የዘረጋናቸውን መልካም እሴቶች ኃላፊነት የማይሰማቸው አካላት በአንድ ጀንበር እንዲንዷቸው ብሎም ወደስርዓት አልበኝነት እንዲቀይሯቸው ፈጽሞ እንደማይፈቅድ እምነቴ ጽኑ ነው፡፡ በምንም መልኩ ቢሆን መንጋዎች እንዲሰለጥኑብን የማንመች ህዝቦች መሆናችንን ደግመን ደጋግመን ማሳየት በቻልንበት ውብ ታሪካችን ውስጥ የሙስሊሙ ማህበረሰብ ሚና አጅጉን የላቀ እንደነበር እሙን ነው፡፡ አሁንም መላው ሙስሊም ወገኖቼ ይህንኑ ሀገርን በስርአት የማቆም ደማቅ ታሪኩን በአብሮነቱ እንደሚያስቀጥል ምንም ጥርጥር የለውም፡፡

መልካምን መውደድ፣ ክፉ ተግባርን ማውገዝ የሁሉም ሃይማኖቶች እሳቤና ዕሴት ነው፡፡ ክፉ ተግባር በአንድ አካባቢ ወይም አጋጣሚ ብቻ በመከሰቱ በፍፁም ዝም ያለማለት ባህላችንን ሙስሊሙ ማህበረሰብ በጠንካራ መሰረት ላይ የማነጽ ታሪኩን አጠናክሮ እንዲቀጥልም አደራ ለማለት እፈልጋለሁ፡፡ እንደ አንድ ሕግ አክባሪ ዜጋ መልካም ተግባርን የመውደድ እና ክፋትን የማውገዝ ኃላፊነት እንዳለብን ባለመዘንጋት የሀገራችንን ሁለንተናዊ ለውጥ በመደመር ለማስቀጠል ሙስሊሙ የሀገሬ ህዝብ የበኩሉን ሁሉ እንዲያደርግም ጥሪዬን አቀርባለሁ፡፡

የእኛ ዝምታ ሌሎች ሕገ-ወጦችን በህልውናችን ላይ የሚያዙ የጎበዝ አለቃ እንዳያደርጋቸው መንቃት የሚገባን ጊዜ ላይ መሆናችንንም በአክብሮት ላስታውሰችሁ አወዳለሁ፡፡ ምሁራን፣ የሀገር ሽማግሌዎችና የእምነት አባቶች የማህበረሰባችሁ የእውቀት ቀንድ ናችሁና ሥርዓት አልበኝነት እንዳይሰለጥን ማኀበረሰባችሁን በሞራልና በሥነምግባር ተግታችሁ እንድታንጹ አደራ እያልኳችሁ የተከበራችሁ የሀገራችን ሙስሊሞች በዚህ ታላቅ እና በመስጠት ጸጋ የተቃኘ ታላቅ

በዓል ወቅት ለእናንተ ለወገኖቼ የመልካም ምኞት መግለጫ ለማስተላላፍ በመቻሌ የተሰማኝን ከፍ ያለ ክብርና ልባዊ ደስታ ልገልጽላችሁ እወዳለሁ፡፡ በመጨረሻም በዓሉ አብሮነታችን የሚፈካ የሚያብብበት፣ ሰላምና ሀገራዊ አንድነታችን ስር የሚሰድበት የበረከት በዓል እንዲሆንላችሁ ከልብ እመኛለሁ፡፡

ኢድ ሙባረክ መልካም በዓል!

ኢትዮጵያ በልጆቿ ጥረት ታፍራና ተከብራ ለዘላለም ትኑር!

ፈጣሪ ኢትዮጵያንና ህዝቦቿን አብዝቶ ይባርክ!