አርቲስት ቴዎድሮስ ካሳሁን በቡራዩና አካባቢዋ ለተፈናቀሉ ዜጎች የ1 ሚሊዮን ብር ድጋፍ አደረገ

ተወዳጁ አርቲስት ቴዎድሮስ ካሳሁን ወይም  በቅጽል ስሙ ቴዲ አፍሮ ከባለቤቱ ጋር በመሆን  በቡራዩና አካባቢዋ ጉዳት ለደረሰባቸው እንዲሁም  ለተፈናቀሉ ዜጎች  የ 1ሚሊዮን ብር ድጋፍ አደረገ ።

አርቲስት ቴዎድሮስ በዛሬው ዕለት ከባለቤቱ ወይዘሮ አምለሰት ሙጬ ጋር በመሆን በመድሓኒአለም ትምህርት ቤት  ተጠልለው  የሚገኙትን   ተፈናቃዮች  በጎበኘበት  ወቅት ነው  የ 1  ሚሊዮን  ብር ድጋፍ ያደረገው ።

አርቲስት ቴዎድሮስ  ተፈናቃዮችን  ከጎበኘ በኋላ  ለዋልታ ቴሌቭዠን እንደገለጸው  በሁኔታው  እጅግ ማዘኑንና  የአዲስ አበባ  ህዝብ  ለተፈናቃዮች  እያደረገ  ላለው  ድጋፍ  ታላቅ ምስጋና ይገባዋል ብሏል ።

አርቲስት ቴዎድሮስ ያደረገውን  የ1 ሚሊዮን  ብር ድጋፍ  የተቀበለው  የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር  በበኩሉ  አርቲስት  ቴዎድሮስ ለተፈናቃዮች  ላደረገው ድጋፍ  ምስጋና አቅርቧል ።

ከቡራዩ አካባቢ ለተፈናቀሉ  ዜጎች  የተሠጠው የ1  ሚሊዮን  ብር ድጋፍም በመድሐኒዓለም  ትምህርት ቤት  ለተጠለሉ  ተፈናቃዮች  አስፈላጊውን  ድጋፍ ለማድረግ እንደሚውል የከተማ አስተዳደሩ ገልጿል ።

እስካሁን ድረስ   በመድሓኒዓለም ትምህርት  ቤት ተጠልለው  ለሚገኙ  ተፈናቃዮች  ከ 3 ሺህ የሚሆን ፍራሽና ብርድ ልብስ  ከአዲስ አበባ  ነዋሪዎች  መሠጠቱም  ተመልክቷል ።        

በቡራዩ ከተማ፣ ከተና አሸዋ ሜዳ አካባቢዎች  በደረሰው አደጋ   እስካሁን ድረስ 12 ሺህ  ያህል  ዜጎች  ከመኖሪያ አካባቢያቸው የተፈናቀሉ ሲሆን 1ሺህ 700 የሚሆኑ በመድሓኒአለም ትምህርት  ተጠልለው  ይገኛሉ ።